08/30/2026
(ዘ-ሐበሻ ዜና) የሰው ልጅ በምድር ላይ የሚያሳልፈው ዕድሜ በዓመታት ብዛት ሳይሆን፣ ለትውልድ ጥሎት በሚያልፈው የማይሽር በጎ አሻራ ይለካል። ላለፉት አርባ ዓመታት የኢትዮጵያውያን ሙስሊሞችን መብት፣ ክብርና አንድነት ለማስጠበቅ ግንባር ቀደም ታጋይ፣ መሪ እና የሕዝብ አገልጋይ የነበሩት ክቡር ሐጂ ነጂብ መሐመድ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል።
ሐጂ ነጂብ በሕይወት ዘመናቸው ከሠሯቸው አንጸባራቂ ታሪኮች መካከል፣ ከዛሬ 25 ዓመታት በፊት ከጥቂት ጓዶቻቸው ጋር በመሆን 'በድር ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ድርጅት'ን መመስረታቸው ግንባር ቀደሙ ነው። የተቋሙ ፕሬዝዳንት በመሆን በማገልገልም፣ ከሀገር ውጭ በሚኖረው የዲያስፖራ ማህበረሰብ ዘንድ ጠንካራ የትስስር፣ የመረዳዳት እና የአንድነት መንፈስ እንዲገነባ የላቀ ሚና ተጫውተዋል። "የበድር ታሪክ ከሐጂ ነጂብ ስምና አስተዋጽኦ ፈጽሞ ተነጥሎ አይታይም" ሲል ተቋሙ ባወጣው የሐዘን መግለጫ የኚህን ታላቅ ሰው ውለታ አስታውሷል።
የሐጂ ነጂብ የትግል ምዕራፍ በተቋም ምስረታ ብቻ የተገደበ አልነበረም። የኢትዮጵያ ሙስሊሞችን የመብት ጥያቄ አንግበው አምባገነን ሥርዓቶችን በድፍረት ከመሞገት ወደኋላ ብለው አያውቁም። በሀገር ቤት የነበረውን የመብት ጥያቄ በማስተጋባት ከወንድሞቻቸው ጋር በመሆን ፊት ለፊት የተጋፈጡ ሲሆን፣ በተለይም በ'ድምፃችን ይሰማ' የመብት ትግል ወቅት ለእስር የተዳረጉትንና ቤተሰቦቻቸውን በክፉ ቀናቸው ከጎን በመቆም ያሳዩት የማይናወጥ አጋርነት በማህበረሰቡ ልብ ውስጥ ለዘላለም ተቀርጾ የሚኖር ነው።
የበድር ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ድርጅት፣ ማህበረሰቡ ይህንን ታላቅ አገልጋይ በሞት በማጣቱ የተሰማውን ጥልቅ ሐዘን ገልጿል። "እኚህ ታላቅ ሰው በአካል ከዚህ ዓለም ቢለዩንም፣ የሠሩት መልካም ሥራ፣ ያስተላለፉት እሴት እና የቆሙለት ዓላማ በትውልድ ልብ ውስጥ ይኖራል" በማለትም ለቤተሰቦቻቸው፣ ለወዳጅ ዘመዶቻቸው፣ እንዲሁም የበድር አባል ለሆነው ፈርስት ሂጅራ ፋውንዴሽን አባላት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሙስሊም ማህበረሰብ መጽናናትን ተመኝቷል።
ኢና ሊላሒ ወኢና ኢለይሒ ራጂኡን! አላህ (ሱ.ወ) ለሐጂ ነጂብ መሐመድ ምሕረቱን አውርዶ በጀነተል ፊርደውስ እንዲያኖራቸው እንመኛለን።