01/24/2023
ሰበር ዜና
በአጣዬ ከተማ ከባድ ተኩስ እንደሚሰማ ነዋሪዎች ተናገሩ!
በሰሜን ሸዋ ዞን የኤፍራታ እና ግድም ወረዳ መቀመጫ በሆነችው አጣዬ ከተማ ከባድ የተኩስ ድምጽ እንደሚሰማ ህይወታቸውን ለማትረፍ እየሸሹ የሚገኙ ነዋሪዎች ተናገሩ።
ነዋሪዎቹ እንዳሉት፣ የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች ወደ ከተማዋ መግባታቸውን ገልጸዋል።
ነዋሪዎቹ አክለውም፣ የፌዴራል እና የክልል የጸጥታ አካላት በከተማዋ ቢኖሩም ቁጥራቸው አነስተኛ በመሆኑ ታጣቂዎቹን ወደ ከተማዋ ከመግባት መከላከል አልቻሉም ብለዋል።
በአራት ዓመት ጊዜ ውስጥ ከስምንት ጊዜ በላይ የኦነግ ሸኔ ጥቃት ሰለባ የሆነችው የአጣዬ ከተማ፤ ዳግም ለጥቃት ተዳርጋለች።
ከሰሞኑ በአማራ ክልል የኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ልዩ ዞን እና ሰሜን ሸዋ ዞኖች የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች በጸጥታ ኃይሎች እና በንፁሃን ላይ ተኩስ ከፍተው መጠነ ሰፊ ጉዳት እያደረሱ ይገኛል።
በአሁኑ ወቅት የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች ወደ አጣዬ ከተማ የገቡ ሲሆን፤ ከባድ ተኩስ እንደሚሰማም ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የከተማው ነዋሪ አረጋግጠዋል።
የፌዴራሉ መንግሥት የከፋ ጉዳተ ሳይደርስ ተጨማሪ ኃይል ወደ ከተማዋ እንዲያሰማራም ነዋሪዎቹ ጠይቀዋል ሲል የአማራ ድምፅ ዘግቧል።