08/26/2026
ኮራንብህ ገዱ!
እውነት እና ሀሰት የየራሳቸው መልክ ቢኖራቸው፤ ሀሰት የስልጣን ጥማት ያሰከራቸውን፣ እነዛን በንጹሐን ደም የጨቀዩትንና የሕዝብን ሀብት የበዘበዙትን አስመሳይ ባለስልጣናት ስትመስል፣ እውነት ግን ዛሬ ላይ የአቶ ገዱ አንዳርጋቸውን ጥርት ያለ ገጽታ ትላበሳለች።*****
ትላንትና ገዱ አንዳርጋቸው በአሜሪካ የፓርኪንግ ስራ ላይ ተሰማርተው የሚያሳይ ቪዲዮ በአንዳንድ ወገኖች ዘንድ እሳቸውን ለማሸማቀቅና ለማዋረድ በማሰብ ተሰራጭቶ ነበር። ነገሩ ግን ተገለበጠ እና ክብርን ሞገሰን ለገዱ አወረደ!****
በመሀይም የተለቀቀው ቪዲዮ የተንኮል ሸረባው ወጥመድ ተሰብሮ ክብራቸውንና ሞገሳቸው ይበልጥ አጎላው፤ ውርደት ያሰቡትም ለሳቸው ያልተሸረፈ የሕሊና ካባ ሆነላቸው። በጭፍን ጥላቻ ገዱን ያገለሉ ሁሉ ዛሬ በገዱ አንዳርጋቸው ንፁህ ህሊና እረኩ!****
በአንድ ወቅት ሀገራቸውን በታላቅ ኃላፊነት ወክለው በዋይት ሐውስ ውስጥ ከዓለም ኃያላን መሪዎች ጋር በክብር የተደራደሩት የቀድሞው የአማራ ክልል ፕሬዝዳንትና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፣ ዛሬ በገዛ ላባቸው ጥረው ግረው ቤተሰባቸውን እያስተዳደሩ መገኘታቸው ትልቅ የሞራልና የቅንነት ማስተማሪያ ነው።****
አቶ ገዱ ህሊናቸውን ቢሸጡ፣ ለስልጣን ቢንበረከኩና እንደሌሎቹ የህዝብን ሀብት ወደ ውጭ ቢያሸሹ ኖሮ፣ ዛሬም በቅንጦት ማማ ላይ ተቀምጠው የዶላር ክምር ያንደላቅቃቸው ነበር። እሳቸው ግን ከውሸት ዝና እና ከደም ገንዘብ ይልቅ ንጹሕ ህሊናን መረጡ።****
በፖለቲካዊ ውሳኔዎቻቸው ዙሪያ ትናንት የነበረን ልዩነት ወይም ቅሬታ ምንም ይሁን ምን፣ የዛሬው እውነታ በአንድ ድምፅ እንድናከብራቸው ያስገድደናል። ይሄ ከፖለቲካም አልፎ ንፁህ ወንጌል ነው። ዛሬ ወንጌል እንሰብካለን የሚሉ ወንጀለኞች በሆኑበት ጊዜ የአቶ ገዱ ህይወታቸው ግን ምስክር የሚሆን የወንጌል ፍሬን ይመስላል!****
በስልጣን ሳሉ ያልሰረቁ፣ ሀገር ያልዘረፉ ወርቅ ያላሸሹ ከማንም ጋር በሙስና ያልተጨማለቁ እና ዛሬም ዝቅ ብለው በማንኛውም የጉልበት ስራ በላባቸው ማደርን የመረጡ እውነተኛ የሕዝብ ልጅ መሆናቸውን በተግባር አሳይተዋል። በድጋሚ ክብር ይገባቸዋል!****
ያ ባለጌ ማንም ይሁን ማንም ገዱን አዋረድኩት ብሎ ያሰራጩት ቪዲዮ ውርደት ሳይሆን የንጹሕ ህሊና የክብር ምስክር ወረቀት ሆነላቸው። ዛሬ ሌሎች በሰረቁት ገንዘብና በሠሩት በደል በየቀኑ በፍርሃትና በጭንቀት እንቅልፍ አጥተው ሲገላበጡ፣ አቶ ገዱ ግን ባልረከሰ ማንነት፣ ቀና ብለው፣ በሰላም ወጥተው በሰላም ይገባሉ።
ክብር ማለት ወንበርና ስልጣን ሳይሆን በራስ ላብና በንጹሕ ህሊና መኖር ነው