05/29/2026
የትምህርት ቤት ትዝታ!
በሰሜናዊ ካሊፎርኒያ የባህል ፣ የንግድ ፣ የፋይናንስ ፣ ና የቴክኖዎሎጂ ማእከል በሆነችው ሳንፍራንሲስኮ ከተማ ነው ያለሁት:: ውቧ #ሳንፍራንሲስኮ በፓስፊክ ውቂያኖስና ሳንፍራንሲስኮ ቤይ መሃል እንደ ፈርጥ ጉብ ያለች ከተማ ናት:: ነዋሪዎቿ ፍሪስኮ እያሉ ሲያቆላምጧት አንዳንዶቹ ደግሞ "The city” ይሏታል:: #ጎልደን ጌት ብሪጅ ፣ የአልካትራዝ አይላንድ ፣ እንዲሁም ኬብል ካሮቿ ፣ ለብዙዎች ጎብኞቿ መስህብ ናቸው:: ውበቷ የጥበብ ዛርን ይቀሰቅሳል:: "ጥበብ ጠራችን" የሚሉት ሰዎች እንዲህ አይነት አካባቢ ሲያዩ ይሆን?:: ለብ ያለው ሙቀት ፣ ና በዙርያዬ ያሉት ዛፎችን ና አልፎ አልፎ ፊቴን እየዳበሰኝ የሚልያፍው ነፋስ ድንገት #ድሬን አስታወሰኝ:: "የበርሃዋ ንግስት" ያስባሏት ዛፎቿ ፣ ትዝታ የሚሆነው የምሽታ አየሯ ሁሉም በተራ በተራ ተመላለሱብኝ:: ድሬዋን ሳስብ የመጀመሪያ በአእምሮዬ የሚመጣው የምሽት አየሯ ነው:: ነገር ግን #ለድሬ ልጅ እንደ ፈትል ቀለም ቢጎለጎል የማያልቅ ብዙ ብዙ ትዝታዎች አሉት:: ትምህርት ቤቷ ፣ አሸዋው ፣ ታይዋኖቿ ፣ ፍራፍሬዎች ፣ ብስኩቶቿ ፣ የጎዳና ምግቦቿ ስንቱን ልጥቀሰው!
#የድሬ ትምህርት ቤቶች በራሳቸው የትዝታ ማህደር ናቸው:: በአንድ አመት ሁለት ክፍል እያለፍኩ(ተርም መታት ይባላል) ስለሆነ አንድም ደግሞ የተለያዩ አካባቢዎች ስለተማርኩ ነው መሰል አንደኛ ደረጃ ላይ ብዙም ትዝታ የለኝም:: አብዛኛው የትምህርት ቤት ትዝታዬ ሚድል ክላስ ላይ ይጀምራል:: #ዲፖ ትምህርት ቤት ምንም እንኳን ዛሬ የድሬዳዋ "ቴክኒክ ኮሌጅ" ጠቅልሎት ታሪኩ ቢጠፋም በወቅቱ እስከ ስምንተኛ ክፍል ከሚያስተምሩ ትምህርት ቤቶች ውስጥ አንዱ ነበር:: ነብሳቸውን ይማረውና ዳይሬክተራችን ጋሽ ታደስ ፣ የሂሳብ መምህራን እትዬ ሂሩት ና እትዬ አሰለፈች፣ የኤሌክትሪክ ሲቲ መምህርና ተግባራዊ ትምህርት በመስጠት የሚታወቁት ጋሽ ከቤ ፣ የታሪክ መምህራችን ጋሹ(ለእኔ ደግሞ ዘመዴ ነው) ፣ የሳይንስ መምህራኖቻችን ጋሽ ዘነበና ጋሽ ግርማ ፣ ጏደኛሞቹ ጋሽ ዳንኤልና ማይክል:: ጋሽ ዳንኤል ጆግራፊ መምህር ሲሆን ጋሽ ማይክል (ብቅ ጥልቅ እንለው ነበር) ደግሞ እንግሊዘኛ ነበሩ:: ከመምህራኖቹ ሁሉ "አራዳ ነን" የሚሉት ሁለቱ ነበሩ:: ምርጡና ኩሩው ጎበዝ የእንግሊዘኛ መምህራችንና የእንግሊዘኛ ክበብ አስተባባሪው ጋሽ አንተነህ፣ ጉልበተኛው የስፖርት መምህር ጋሽ አሸብር ና የእርሻ መምህራችን ጋሽ ምትኩ (ዘንጋዳ) ከማልረሳቸው መምህራን ውስጥ ናቸው::
እትዬ ሂሩትና እትዬ አሰለፈች
ሁለቱም ምርጥ የሂሳብ መምህራን ናቸው:: ሂሳብን አቡክተው ይጋግሩታል 😂 :: እትዬ ሂሩት ጠይም ደርባባ ስትሆን ሁሉ ነገሯ እንደ አንድ ጠንካራ እናት ነው:: በርህራሄ የተሞላው አስተያየቷ ፈቅደህ እንድታከብራት የሚያስገድድ መግነጢሳዊ ኃይል አለው:: በዛው ልክ ቁጣዋ እንደ እሳት ይጋረፋል:: በሷ ክፍለ ጊዜ መረበሽ የማይታሰብ ነው! በተለይም በሌሎች ክላሶች በማወክ የሚታወቁ የነበሩ የዛን ጊዜ ጎረምሶች እነ ጥሌ ፣ እነ ቢተው ፣ እነ ሚኪያስ በእርሷ ክፍለ ጊዜ ከእነ መኖራቸውም አይታወቅም:: ይሄ ባህርይዋ ከክፍል ውጭም ያው ነው:: አንዴ ማንም ቀና ብሎ የማያየውን ጥሊን ምን እንዳጠፋ አላውቅም የዩኒፎርም ኳሌታዎቹን ጨምድዳ እየጎተተች ወደ ቢሮ ስትወስደው ትዝ ይለኛል:: 4 ሰው የሚያንከባልለው ጥሌ እንደ በግ እየተጎተት ሄደ እንጅ በሌሎች እንደሚያደርገው እንኳን ሊናገራት ልብሱን ለማስለቀቅ እንኳን አልደፈረም:: ፍቅር ናት ፣ እናት ናት ፣ መምህር ናት በዚያው ልክ ደግሞ ከተቆጣች ሁሉም የሚገዙላት ኃያል ነበረች:: እትዬ ሂሩት በሗላ ላይ ትምህርቷን አሻሽላ ወደ ትልቁ ሃይስኩል ገብታ ነበር:: በሗላ ግን በኢትዮጵያ አየር መንገድ ሴኩሪቲ ክፍል እንደተቀላቀለች እራሴው አግኝቻታለሁ:: ዩንቨርስቲ ከጨረስኩ በሗላ ድሬዳዋ በምሰራበት ጊዜ ለስራ ወደ አዲስ አበባ ለመሄድ ኤርፖርት ፍትሻ ላይ ተገናኝተናል:: አቤት ደስታዋ! ልጇ እንጅ ተማሪዋ አልመስልም! ስራዋን ትታ ጥምጥም ብላ የደስታ ሳግ እየተናነቃት ሳመችኝ! ጥሩ መምህራን የተማሪዎቻቸው ስኬት የደስታቸውም ጥግ ነው:: እትዬ አሁን የት እና እንዴት እንዳለች አላውቅም:: ይሄን የሚያነብ ና የሚያውቅ ቢያጋራን ውለታን እመልሳለሁ:: Yonatan Solomonየምታውቀው ካለ ብታጋራን ደስ ይለኛል::
ሌላዋ ምርጥ መምህራችን እትዬ አሰለፈች ናት:: ከእትዬ ሂሩት ጋር የሚያመሳስላቸው ሁለቱም የሂሳብ መምህራን መሆናቸው ብቻ ነው:: ፍፁም ይለያያሉ! እትዬ አሰለፈች ከአረማመዷ እስከ ንግግሯ ቀስ ብሎ እንደሚወርድ ኩልል ያለ ውሃ ነው:: ቀጭን ረዘም ያለች ጠይም መልከ ቀና ስትሆን እርጋታዋ እንደ ወረርሽኝ ይጋባል:: ከእርሷ ጋር ሲያወሩም ይሁን በክፍለ ጊዜዋ ሁሉም በእርጋታና በፅሞና እንዲከታተሏት የሚያደርግ ልዩ ተሰጥኦ አላት:: እትዬ የቤተክርስቲያን ልጅ ናት:: የማህበረ ቅዱሳን አባል! የት ቤተክርስቲያን እንደምትሄድ አሁን ትዝ ባይለኝም እኔም ያንጊዜ የደብረ ምህረት ቅዱስ ሚካኤል ሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን አባል ስለነበርኩ በየንግሱ አልፎ አልፎ አያት ነበር:: አይን ላይን ከተጋጨን በስስ ፈገግታዋ ታበረታታኝ ነበር:: እትዬ አሰለፈች አስረድታ ስትጨረስ “If you have Any question or any doubts you’re welcome” የምትላት ነገር በብዙዎቻችን የቀረች አባባል ነች:: ልክ እንደ እትዬ ሂሩት እትዬ አሰለፈችም በሗላ ሃስይስኩል ተገናኝተናል:: በጊዜው የሃስይስኩል የሂሳብ መምህራን ውስጥ አንዱ ከሆነው መምህር ደስታ ጋር በጋብቻ ተጣምረው እንደሚኖሩ ብሰማም አሁን ያለችበትን ሁኔታ ግን አላውቅም:: የትዬን ሁኔታ የሚያውቅ ሰው ቢያካፍለን ደስታችን ወደር የለውም:: ይቀጥላል................