05/22/2026
ግንቦት13 1983 ዓ/ም ኮ/ል መንግስቱ ኃማርያም-- ባለ መልካም ስብዕናው የኢትዮጵያ ሰራዊት--አውቶብስ ተራ
✍️✍️✍️
በዕለቱ የጠዋቱን ስራችንን አከናውነን እኔ ሹልኬ ምግብ ቤት በ1 ብር ሹሮዬን በልቼ ከሎንችናው የሗላ ወንበር አረፍ እንዳልኩ ከአጎናፍር ሆቴል ጋሽዬ ከ 2 ጓደኞቻቸው ጋር ሆነው በር አንኳኩ… ያለ ሰዓታቸው።
✍️
ሹልኬ ከትልቁ መናኻሪያ አጥር መጨረሻ ገባ ብሎ በሁለት ጠባብ ግድግዳዎች ተሾልኮ የሚገባበት ሽሮ ከፈለከው ቃሪያ ጋር እና ቀዝቃዛ ውሃ በኒኬል የሚቀርብበት አሪፍ ቤት ነበር።
አጎናፍር ሆቴል ደግሞ ኸዚሁ መነኻሪያ ፊት ለፊት የሚገኝ ሲሆን በወቅቱ በሥጋው በተለይም በቅቅሉ እንዲሁም በጠጁ ይታወቃል። በተጨማሪም ከረንቡላ ወዳጆችም ያዘወትሩታል።
✍️
ያለ ሰዐታቸው መምጣታቸው ግር ብሎኝ በር ከፈትኩና ወደ ወንበሬ ስመለስ
“…ሰማህ አንተ ልጅ…” አሉኝ
“..አቤት ጋሽዬ..”
“..ሰውዬው ከዳን…”
“..ማን ነው..”
“.. መንግስቱ ኃ/ማርያም ጥሎን ወጣ..”…
የመድሃኒያለም ያለህ❗️
✍️
ጋሽዬ የአሽከርካሪ ወንበር ላይ, ጓደኞቻቸው አንዱ ሞተር ላይ አንደኛው ጋቢና ሆነው ብዙም የማይሰማኝ ጭውውት ይዘው ከቆዩ በሗላ ተመልሰው ለመሄድ እየተዘጋጁ አንተ ልጅ ምሳ በልተሃል ሲሉኝ መብላቴን ገልጬ ወደ ሗላ ወንበሬ ተመለስኩ።
✍️
የፕሬዝዳንቱ መውጣት ከተሰማ ከሰዓታት በሗላ አምቦ የነበረው ሰራዊታችን በሁለት ረድፍ ከመሰላሚያ አቅጣጫ አውቶብስ ተራ ደረሰ።
ይህ ሰራዊት ከቀናት በሗላ የራሴ የሚለው ነገር እንደማይኖር አያወቀ፤ በበረኸኞቹ ምን ሊያደርሱባቸው እንደሚችሉ ባላወቁበት ሁኔታ ፤ ነገር ግን ባላቸው የፀና ኢትዮጵያዊነትና ከዚህም በመነጨ ከፍ ያለ ሞራል ከፍ ያለ ንግድ የሚከወንበትን አውቶብስ ተራን እና መርካቶን በሚገርም .....በሚገርም... እና ታሪክ ሲያስታውሰውና ሲዘክረው በሚኖር መልካም ስነ- ምግባር አምስት ሳንቲም ሳያነሳ አለፈ❗️...አምስት ሳንቲም ❗️
✍️
ያ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን የቆመ ሰራዊትን ለረጅም ጉንቦት 20ዎች “.. የደርግ ሰራዊት “ እያሉ በETV ይዘባበቱበት ነበር።
✍️✍️✍️
ዘላለማዊ ክብር ለኢትዮጵያ ሰራዊት ❤️
ከሠላምታ ጋር
✒️
ሀብታሙ ሽፈራው