01/05/2026
(ዘ-ሐበሻ ዜና) የኢራኑ ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻመኔኢ ሀገራቸው የኒውክሌር እና የሚሳኤል አቅሟን በከፍተኛ ጥንቃቄ እንደምትጠብቅ አስታወቁ። በተጨማሪም በቀጠናው ለሚታየው አለመረጋጋት የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን በዋና ተጠያቂነት የፈረጁ ሲሆን፣ የፋርስ ባህረ-ሰላጤ ወደፊት ከአሜሪካ ነጻ እንደሚሆን ተነበዋል።
ዶናልድ ትራምፕ የኢራንን የጦር መሳሪያ እና የኒውክሌር አቅም ለማዳከም ወይም ለማፍረስ ያላቸውን ፍላጎት ተከትሎ፣ ኻመኔኢ ጠንከር ያለ ምላሽ ሰጥተዋል። ኢራናውያን የኒውክሌር እና የሚሳኤል አቅማቸውን እንደ ትልቅ "ብሔራዊ ሀብት" እንደሚቆጥሩት የገለጹት መሪው፤ "ልክ እንደ የውሃ፣ የየብስ እና የአየር ድንበሮቻችን ሁሉ ይህንንም አቅማችንን በጽኑ እንጠብቀዋለን" ብለዋል።
በቅርቡ አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ያደረሱትን ጥቃት እና ቴህራን በቀጠናው ባሉ ሀገራት ላይ የወሰደችውን እርምጃ ተከትሎ ለተፈጠረው አለመረጋጋት፣ ኻመኔኢ የአሜሪካን ወታደራዊ መገኘት ተጠያቂ አድርገዋል። በመካከለኛው ምስራቅ ላለው የጸጥታ መደፍረስ ቁልፉ ምክንያት "የአሜሪካ ባዕዳን ኃይሎች በፋርስ ባህረ-ሰላጤ መመስረታቸው ነው" ሲሉ ወቅሰዋል።
አክለውም አሜሪካ በቀጠናው ያሏትን የጦር ሰፈሮች "አሻንጉሊት" ሲሉ የጠሯቸው ሲሆን፣ "እነዚህ ሰፈሮች የራሳቸውን ደህንነት እንኳ ማስጠበቅ የሚችሉበት አቅምም ሆነ ጥንካሬ የላቸውም። ስለዚህ አሜሪካ በቀጠናው ላሉ ጥገኞቿ እና ወዳጆቿ ደህንነትን ታረጋግጣለች ብሎ ተስፋ ማድረግ አይቻልም" ሲሉ አጣጥለውታል።
የሆርሙዝ ስትሬት ታሪካዊ ዳራን ያነሱት ሞጅታባ ኻመኔኢ፣ ቦታው ባለፉት ክፍለ ዘመናት (እ.ኤ.አ. በ1622 የፖርቹጋል ጦር መባረርን ጨምሮ) የበርካታ ኃይሎችን ስግብግብነት የቀሰቀሰ መሆኑን አስታውሰዋል።
ሆኖም ከየካቲት ወር መገባደጃ ጀምሮ በአሜሪካ እና እስራኤል የተቀሰቀሰውን ጦርነት ተከትሎ የኢራን ኃይሎች ያሳዩትን ጽናት፣ ንቃት እና ደፋር ተጋድሎ ህዝቡ በዓይኑ ማየቱን አድንቀዋል። ጠቅላይ መሪው ንግግራቸውን ሲያጠቃልሉም፣ "የፋርስ ባህረ-ሰላጤ ብሩህ ዕጣ ፈንታ፣ አሜሪካ የማትኖርበት እና ለህዝቦቿ እድገት፣ ምቾት እና ብልጽግና የምትውልበት አካባቢ መሆን ነው" ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።