06/01/2026
ጫማ ጠራጊው ሙሳ
ሰምኑን ሜቄዶኒያ ወደተባለችው ሀገር ተጉዤ ዋና ከተማዋ ስኮፒዬን እየጎበኘሁ በሀውልቶች የተከበበችው ይህቺ ከተማ ላይ ይህንን የጫማ ጠራጊ ሀውልት አይቼ ቀልቤን ስቦት ወደ ሀውልቱ ተጠጋሁ ሀውልቱ ሙሳ የተባለ በከተማዋ ይኖር የነበረ ጫማ ጠራጊ ነበረ። ከሁሉም ጋር ተግባቢ ተወዳጅ ከ 30 አመት በላይ በከተማዋ የኖረ እንደሆነ አስጎብኚዬ ነገረኝ። " እኛ ሀገር ምሁሩ ፖለቲከኛው እና ተዋጊው ብቻ አይደለም እኮ ሁሉም ሰው የራሱ ታሪክ አለው" አለኝ። እውነት ነው ሁሉም የራሱ ታሪክ አለው።
ጫማ ጠራጊውም ታሪክ አለው ስንቱ ወደ እጮኛው ሲሄድ ጫማውን አሳምሮ ሸኝቷል ስንቱ ሀላፊ ወደ ቢሮው ሲገባ ጫማውን አስውቧል የስንቱን ጫማ ሰፍቷል በስንቱ ተመስግኗል። ስንት የተበሳጨ ሰው ጫማ እያስጠረገ ብሶቱን ነግሮታል ስንቱ በንቀት አይቶታል ስንቱ አባሮታል ስንቱን አመስግኗል ብዙ ብዙ ሁሉም ታሪክ አለው። ሀገረ ሜቄዶኒያ በዋና ከተማዋ ስኮፒዬ የተመሰገነውን ተወዳጁን ሙሳ በህይወት ባይኖርም እንደ ምልክት በማድረግ ጫማ ጠራጊዎችን ሁሉ የሚወክል ይህንን ሀውልት አቁማለች ።
ብዙ ሀገራት ተጉዣለሁ በሺ የሚቆጠሩ ሀውልቶች አይቻለሁ ሁሉም ማለት በሚያስደፍር ሁኔታ መሪዎችን ተዋጊዎችን ታሪካዊ ክስተትን የሚዘክሩ ናቸው። ይህንን ስመለከት ታዋቂው አሜሪካዊ ጸሐፊና አስተማሪ ቡከር ቲ የተናገራት ትዝ አለቺኝ "ግጥም በመጻፍ በመዋጋት ሀገራ በመምራት ውስጥ እንዳለው ሁሉ በማንኛውም የጉልበት ሥራ ውስጥም እኩል ክብር እንዳለ እስካልተረዳን ድረስ እንደ ሕዝብ መቆም አንችልም።" እውነት ነው እንደ ሙሳ የሰፈራችን ድምቀት የሆኑ ስንት ሰዎች አሉ ብዙ ።
አመሰግናለሁ!
አቤል ብርሀኑ (የወይኗ ልጅ)
የጉዞ ማስታወሻዬ
ሰሜን ሜቄዶኒያ 2018 ዓ.ም