09/06/2026
የዳዬ - ግርጃ - መልካደስታ እና መለያ - መጆ የአስፋልት ኮንክሪት መንገድ ግንባታ ፕሮጀክት ባጠረ ጊዜ ለማጠናቀቅ እየተሰራ ነው
አዲስ አበባ፣ ሰኔ 2፣ 2018 (ኢመአ)፦ የሲዳማ እና የኦሮሚያ ክልሎችን በመንገድ የሚያስተሳስረው እና 65 ኪሎ ሜትር የሚሸፍነው የዳዬ-ግርጃ - መልካደስታ እና መለያ -መጆ የአስፋልት ኮንክሪት መንገድ ግንባታ ፕሮጀክትን በአጠረ ጊዜ ለማጠናቀቅ እየተሰራ ይገኛል።
ከአጠቃላይ የግንባታ ሥራው አሁን ላይ 63 ነጥብ 4% በመቶው የተጠናቀቀ ሲሆን የአስፋልት ንጣፍ ፣ አፈር ቆረጣ እና ሙሌት ፣ የድሬኔጅ ስራዎች ፣ ሰብ ቤዝ ንጣፍ ፣ ቤዝ ኮርስ ንጣፍ እንዲሁም በርካታ የስትራክቸር ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛል።
የመንገድ ግንባታ ፕሮጀክቱ መነሻውን በምስራቃዊ ሲዳማ ዞን ውስጥ ከሚገኘው ዳዬ ከተማ አድርጎ እስከ ግርጃ/መልካ ደስታ እና መጆ ከተማ ድረስ የሚዘልቅ ነው ።
ለግንባታ ማስፈጸሚያ የሚውለውን ገንዘብ 1,555,708,167.88 (አንድ ቢሊዮን አምስት መቶ ሃምሳ አምስት ሚሊዮን ሰባት መቶ ስምንት ሺህ አንድ መቶ ስልሳ ሰባት ብር ከሰማንያ ስምንት ሳንቲም) በኢትዮጵያ መንግስት ነው የሚሸፈነው ።
ግንባታውን ቻይና ቲሲጁ ሲቪል ኢንጂነሪንግ ግሩፕ የተባለ የሥራ ተቋራጭ በማካሄድ ላይ የሚገኝ ሲሆን ፣ የማማከሩንና የቁጥጥሩን ሥራውን ደግሞ ስታዲያ ኢንጂነሪንግ ወርክስ ኮንሰልታንት በማከናወን ላይ ይገኛል።
የዚህ መንገድ ፕሮጀክት ደረጃውን በጠበቀ አስፋልት መገንባቱ ለአካባቢው ማህበረሰብም ሆነ ለመስመሩ ተጠቃሚዎች ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ እድገት ላይ ከፍተኛ ለውጥን ያመጣል።
ይህ የመንገድ ፕሮጀክት ተገንብቶ ሲጠናቀቅ በአካባቢው የሚመረቱ እንደ ቡና፣ እንሰት፣ እንዲሁም የተለያዩ ማዓድናትን ወደ ገበያ ለማቅርብ ምቹ ሁነታ ይፈጥራል።
በተጨማሪም በተሽከርካሪ ለመጓጓዝ ይወስድ የነበረውን የ 4 ሰዓት የጉዞ ጊዜ ወደ 1 ሰዓት ከማሳጠሩም ባለፈ የትራንስፖርት ተጠቃሚዎችን አላስፈላጊ እንግልት ያቃልላል።
በመስመሩ ላይ ያሉ ከተሞችን ከማስተሳሰሩም ባለፈ የከተሞችን እድገት ያፋጥናል።
የመንገድ ግንባታው በከተማ 21 ሜትር፣ በገጠር 10 ሜትር የጎን ስፋት እንዲኖረው ተደርጎ እየተገነባ ይገኛል ።
ምንጭ፣ ኢመአ