19/06/2026
በአባላት ገቢ አሰባሰብ የታዩ ክፍተቶችን በቁጭት ለመሙላትና የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎትን ለማጠናከር የሚያስችል የግምገማ መድረክ ተካሄደ።
የባህር ዳር ከተማ አማራ ወጣቶች ማህበር የ2018 ዓ.ም የክረምት ወራት በጎ አድራጎት ስራዎች ዝግጅት እና የአባላት ገቢ አሰባሰብ ዙሪያ ያተኮረ ሰፊ የግምገማና የዕቅድ ትውውቅ መድረክ አካሂዷል።
በባህር ዳር ከተማ ወጣቶች ማዕከል በተካሄደው በዚህ መድረክ ላይ የአማራ ወጣቶች ማህበር አመራሮችና፣ አጋር አደረጃጀት አመራሮች የከተማውና የሁሉም ክፍለ ከተማ የወጣቶች መሪዎች ተገኝተዋል።
ማህበሩ በ2018 ዓ.ም ወጣቱን በማህበራዊና በኢኮኖሚያዊ ዘርፎች ተጠቃሚ ለማድረግ ያከናወናቸውን ተግባራት የገመገመ ሲሆን በሁሉም ክፍለ ከተማ የሚገኙ የማህበሩ መዋቅሮች እስካሁን ስላላቸው የአባላት ቁጥርና አጠቃላይ አፈፃፀም ሪፖርት አቅርበዋል።
አመራሮቹ በቀጣይ በተለይም በክረምት ወራት የሚከናወኑ የበጎ አድራጎት ስራዎችን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ ወጣቱን በንቃትና በባለቤትነት ስሜት ማሳተፍ እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል።የባህር ዳር ከተማ ወጣቶች ማህበር በአሁኑ ወቅት በከተማ ደረጃ 12,750 የወጣት አባላት መዋቅር እንዳለው በመድረኩ ተገልጿል።
የማህበሩ ፕሬዝዳንት ወጣት ጋሻው አዘነ ባደረጉት ንግግር፤ ከተማዋ ያላትን ሰፊ አቅም ያህል የአባላት ገቢ አሰባሰብ አፈፃፀሙ ከሌሎች የክልሉ ከተሞች ጋር ሲነጻጸር ዝቅተኛ መሆኑን ጠቁመዋል። ፕሬዝዳንቱ አክለውም“ይህ አፈፃፀም ከከተማዋ ስምና ከወጣቱ ቁጥር ጋር የማይመጥን በመሆኑ፣ በቀሪዎቹ ጊዜያት ያሉትን ተግዳሮቶች በቁርጠኝነት በመፍታት እያንዳንዱ መዋቅር የበኩሉን አስተዋጽኦ ማበርከት ይኖርበታል” ሲሉ አሳስበዋል።
በግምገማ መድረኩ ላይ ማህበሩን በፋይናንስና በአደረጃጀት ረገድ ይበልጥ ለማጠናከር በገቢ አሰባሰብ ስራ ላይ ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንደሚገባ ጠንከር ያለ አቅጣጫና መመሪያ ተቀምጧል። ለዚህም ስራ ስኬታማነት ተደጋጋሚ ድክመት የሚያሳዩና ዝቅተኛ አፈፃፀም ያላቸው የክፍለ ከተማም ሆነ የከተማ ደረጃ አስተባባሪዎች ላይ የአመራር መተካካት እርምጃ እንደሚወሰድ በግልፅ ተመልክቷል።
የአማራ ክልል ወጣቶች ማህበር ዋና ፀሀፊ ሙላት ባይሌ ለማንኛውም ተቋማዊ ስኬት መሰረቱ ጠንካራ ስራ አስፈፃሚና የማይናወጥ መዋቅር መሆኑን አስገንዝበዋል። ዋና ፀሀፊው “ጠንካራና ቁርጠኛ አመራር ሲኖር ማንኛውንም ዕቅድ አቅዶ ስኬታማ ማድረግ ይቻላል፤ ስለሆነም አሁን ካለው ነባራዊ ሁኔታ አንጻር ከመቼውም ጊዜ በላይ በቁርጠኝነትና በትጋት መስራት ይጠበቅብናል” ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
የባህር ዳር ከተማ ወጣቶች ማህበር ዋና አስተባባሪ ወጣት በላይነህ በበኩሉ፣ የ2018 ዓ.ም የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎትን በተመለከተ ማህበሩ በከተማ ደረጃ ሊያከናውናቸው ያቀዳቸውን ስራዎችና ዝርዝር ዕቅድ አቅርቧል። ዋና አስተባባሪው በአፈፃፀም ዙሪያ የታዩትን ክፍተቶች አስመልክቶ ሲያብራራ፡ “ይህ ዝቅተኛ አፈፃፀም ወድቀን የምንቀርበት ሳይሆን፣ ይበልጥ በቁጭት ተነሳስተን ጠንካራ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎችን የምንሰራበት ማነቃቂያ ነው፤ በቀሪው ጊዜ የሚጠበቅብንን የአባላት ክፍያ በአግባቡ በማሰባሰብ የማህበራችንን ግብ እናሳካለን” ሲል ተናግሯል።
ዘጋቢ፥ያደለው ጌጡ
አማራ ወጣቶች ማህበር ቤተሰብ ይሁኑ!
website :-https://aya.org.et/
Facebook
amharayouthheadofficehttps://www.facebook.com/
Youtube:- https://www.youtube.com/
Tiktok:-
WhatsApp:- https://whatsapp.com/channel
Telegram :- https://t.me/ayacommunication
የተደራጁ ወጣቶች የልማት አቅም ናቸው!