30/05/2026
ቃል ቅምሻ ፫
ምነው እስራኤልን የሚያድን ከጽዮን በወጣ!
እግዚአብሔር የሕዝቡን ምርኮ በሚመልስበት ጊዜ፣
ያዕቆብ ደስ ይበለው፤ እስራኤልም ሐሤት ያድርግ።
መዝሙር 14፥7
እስራኤልን የሚያድን የሚመጣው ከጽዮን ነው ። ጽዮን የአዳኙ መገኛ ነው ። ለጽዮን ከተሰጡ ትርጉሞች ሁሉ በዚህ ክፍል የተገለጸው "ጽዮን " የእግዚአብሔርን ሰማያዊ መንግሥት ይገልጻል ።
እስራኤላዊያንን የሚያድን መምጫውም ሰማያዊ ከሆነው መንግሥቱ የሚመጣው እግዚአብሔር ነው ። ዛሬም ማዳኑ ለእስራኤል ብቻ ሳይሆን በምድር ላሉ የሰው ልጆች ሁሉ በክርስቶስ ኢየሱስ በኩል በመስቀሉ ታይቷል ። እግዚአብሔር ወልድ ጌታችን ኢየሱስ ፍጹም መለኮት ሲሆን ነገር ግን የባርያን መልክ በመያዝ ፤ ፍጹም ሰው ሆኖ ለመስቀል ሞት እንኳን በመታዘዝ ለሰው ልጆች የማዳን ሥራውን ገልጧል ። መልአኩም ለዮሴፍ በሕልም ተገልጦ ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና ስሙን "ኢየሱስ "ብለህ ትጠራዋለህ ። "ማለቱ ምነኛ ድንቅ ብስራት ሆኖት ይሆን ?!
ምነው ሕዝቡን የሚያድን ከጽዮን በመጣ "በሚያስበል የኃጢአት ባርነት ተገዝተን ለኖርን ድኩማን የአዳኙ መገለጥ ምነኛስ ደስ ሚያስኝ ዜና ይኾን! በርግጥ ከዚህ የሚልቅ ደስታ የለም ። ዘማሪው እስራኤልን የሚያድን መስፍን የፈለገው ከጽዮን እንጂ ከሌላ ሥፍራ አልነበረምና እኛም የሚያድነውን መስፍን ከጽዮን ከላይ ከሰማይ እንሻ ።
በሌላ መዝሙር ላይ "ዐይኖቼን ወደ ተራሮች አነሣሁ ፣ ረዳቴ ከወዴት ይምጣ ፤ ረዳቴ ሰማይና ምድርን ከፈጠረ ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው ። "እንዳለ ዐይናችንን ሊከልልለን ከሚችለው ተራራ ይልቅ የሁለ ፈጣሪና ጌታ የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር ላይ እናድርግ ። ረድኤት ማዳን ያለው ከርሱ ዘንድ ነውና ። የማዳን ሥራውን በተግባር ሲገልጥ የሕዝቡን ምርኮ መመለስ መገለጫው ነው ።
የሕዝቡ ምርኮ መመለስ የተነፈገውን ነጻነትና መብት መልሶ መጎናጸፉ ነው ። ምክንያቱም የባርነት መገለጫው ነጻነትና መብትን መነፈግ ነው ። የሚያድነው ንጉሥ ሲመጣ ፤ ከባርነት ዋጅቶ ነጻነትና መብትን ለሕዝቡ ይሰጣል ። ይህም በክርስቶስ ለሚያምን ሁሉ ሆኗል ደግሞም ይሆናል ።
የእስራኤል ልጆች በእውነተኛ ደስታ የሚመሉትና ሐሤት ሚያደርጉት ፤ ማዳን ከጽዮን ሲመጣ ፣ ምርኮንም ከጽዮን የሚመጣው እግዚአብሔር ሲመልስላቸው ነው ። እውነተኛ ሐሤትና ደስታ የእግዚአብሔር ሕዝብ የሚያገኘው በእግዚአብሔር እና ከእግዚአብሔር በሚሆን ነገር ነው ።
እግዚአብሔርን እና ከእግዚአብሔር ዘንድ የሆነውን በመሻት እንድንኖር ጸጋው ይብዛልን !!
✍️ጌታሁን አያኖ