21/04/2026
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየቸገረህ ያለው ብትሉኝ አቋም በሚፈልጉ ግልጽ ጉዳዮች ላይ ሆነ ብለው አቋም ላለመያዝ አቋም የያዙ ሰዎች! እጃቸውን ዘርግተው ማትጨብጧቸው Ghost የሆኑ፤ መስመር የሌላቸው ሰዎች አሉ።
ከቅርብ ጊዜ የመጣው አዲሱ ስትራቴጂ፤ አቋም ሳይይዙ መንሳፈፍ ነው። ለምን? ሁሉም ቤት ጣሪያ ላይ ማረፍ ያስችላል። ለዛ አዋጭ ነው። A ም ነኝ ደግሞም Z ም ነኝ። ከዚህ ከ A ጋር ፀብ የለም ከ Z ም ጋር ፀብ የለም፤ የሁሉም ወዳጅ ሆናችሁ መሄድ ከፈለጋችሁ፤ መንገዱ ውስብስብ አይደለም፤ አቋም አይኑራችሁ። በሁሉም ቤት አባወራ ላይ ዘፍ የሚል አሞራ ነው ምትሆኑት።
መንፈሳዊ ብስለት ወንድሞቼ እህቶቼ፤ ተንሳፋፊ አያደርግም። በዶክትሪን ግንባታ ውስጥ አልፎ ማደግ አቋም የለሽ አማኝ አያደርግም። ተፍገምጋሚ ተንገዋላይ አያደርግም። እንደዛ የሚያደርግም አስተምህሮአዊ ምክር ቅዱሳት መጻሕፍት የላቸውም። የእግዚአብሔር ቃል ምክር የሐዋርያት ትምህርት እርስ በእርስ ፈጽሞ የማይጣጣሙ የተቃረኑ ስድስት እና ሰባት አቋሞች ውስጥ እንዲሁ እየፈሰሳችሁ እንድትሄዱ የሚፈቅድ ምክር የላቸውም። ጤናማ ዶክትሪን እንደ መልህቅ ይይዛል። አንዴ ወደ ፊት አንዴ ወደ ኋላ አያስኬድም። ወዲያና ወዲህ አቅጣጫ የለም! ፖዚሽን የለም! ግራውንድ የለም! እንደሱ የሚያደርግ የአስተምህሮ አቀራረጽ የለም። ጤናማ ዶክትሪን እንደዚህ አያደርግም።
በአስተምህሮ መሬት የረገጠ ሰው ጽኑ ነው። ሀሰት ከየትም ይምጣ ከየትም አያፍገመግመውም። ከሁሉም ጋር ጎረቤት አይደለም! ቢቻላችሁ ነው ከሰው ጋር በሰላም ኑሩ የተባለው ስለማይቻል ነው። ከቻላችሁ ጥሩ፤ ግን አይቻልም። ሐዋርያትን ወንጌል ከሁሉም ሰው ጋር ሲያወዳጃቸው አናይም ። ዘመዳቸው ከቃሉ ጋር ዘመድ የሆነ ሰው ነው። ከቃሉ ጋር በግልጽ ጠብ የወጣን ሰው ጎረቤት የሚያደርግ አስተምህሮ ቀረጻ ብሎ ታሪክ የለም። ለምን የሰማይ ስባሪ አያክሉም። ከመላእክት ጋር ቡና እየጠጡ የሚወርዱ ሰዎች ለምን አይሆኑም! እሚፍገመገሙ ከሆነ ተንሳፋፊዎች ናቸው! ተጠበቋቸው። ጤናማውን አስተምህሮ፤ ከሀሰት ትምህርት ለይቶ ማወቅ የመንፈሳዊ ብስለት ምልክት ነው። በእግዚአብሔር ቃል ተኮትኩቶ የማደግ ምልክት ነው።ይሄ ሀሰት ነው! ይሄ እውነት ነው ማለት። ይሄ ጨለማ ነው ይሄ ብርሃን ነው ማለት። ሰኞን ሰኞ እንደምንል፤ ማክሰኞንም ማክሰኞ እንደምንል፤ አንዳንዱን ትምህርት አንዳንዱን እንቅስቃሴ አንዳንዱን ጎራ፤ አንዳንዱን ስብስብ ይሄ ከሰይጣን ነው፤ ይሄ ከክርስቶስ ነው ማለት ይጠበቅብናል።
ስለዚህ በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ከንግዲህ ህጻናት መሆን አይገባም። ይሄ የሐዋርያው የጳውሎስ ምክር፤ ለኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ፤ ከዘመናት በኋላ የኤፌሶንን ቤተ ክርስቲያን ጠቅሟት ነው ያየነው።
ሐዋርያት ሳይሆኑ ሐዋርያት ነን የሚሉትን መርምረህ ሐዋርያ እንዳልሆኑ ደርሰህባቸዋል። ይህንን አደንቅልሃለው ብሏቸዋል ጌታችን። ይሄ ሐዋርያዊ ትምህርት ተጽፎ ስለተሰጣቸው፤ እንዲህ ባለ አስደናቂ ምክር ተገርተው ስላደጉ፤ ሐዋርያ ያልሆነውን ሐዋርያ አይደለህም ብለው ዞር ያደርጉት ነበር።
መንፈሳዊ መደባለቅ፤ ጎራ መደባለቅ በበዛበት የትምህርት አውራቂስ፤ የሀሰት ማዕበል፤ የብዙዎችን ታንኳ እየመታበት ባለበት በዚህ ዘመን ውስጥ፤ ሰዎችን ከእውነት መንገድ ዞር የሚያደርጉ፤ መጽሐፍ እንደሚል የአንዳንዶችን እምነት የሚገለብጡ፤ እምነት ገልባጮች እውነቱን ከላይ አሳይተው ሀሰትንና መርዝን ከታች አስርገው፤ አሽሉከው የሚያስገቡ በበዙበት በዚህ ዘመን፤ የመስቀሉ ስር ቁማርተኞች gamblers በረቂቅ ተንኮል እንደወጣ ቁማርተኛ፤ በወንጌል ላይ ቁማር ለመስራት የወጡ ሰዎች የመድረክ ላይ አፈ ቀላጤነትና ጮሌነታቸውን ተጠቅመው ብዙ የዋሆችን በእግዚአብሔር ቃል ያላደጉትን የሚያስቱ ሰዎች፤ በጾታ በቀለም በበዙበት በዚህ ዘመን ውስጥ እንደ ህጻናት መሆን አያስፈልገንም።
በአስተምህሮ ንፋስ ወዲያና ወዲህ መፍገምገም አያስፈልገንም። በማዕበል ወደ ፊት ወደ ኋላ መሄድ አያስፈልገንም። ከመንፈሳዊ ሕፃንነት መውጣት አለብን። በእግዚአብሔር ቃል በሐዋርያቱ ምክር በተቀበልነው በዚያ አንድ ሃይማኖት እስከመጨረሻ ጸንቶ የመቆም ቁርጠኝነት እያንዳንዳችን ይጠበቅብናል። እግዚአብሔር በሰማያዊ ስፍራ እግዚአብሔር በመንፈሳዊ በረከት ሁሉ ከባረካችሁ በፊቱ ቅዱሳንና አለ ነውር ትሆኑ ዘንድ አለም ሳይፈጠር በክርስቶስ ኢየሱስ በፍቅር ከመረጣችሁ እንደ በጎ ፈቃዱ አስቀድሞ ከወሰነን በክርስቶስ ኢየሱስ ህያዋን ካደረገን በሐዋርያትና በነቢያት መሰረት ላይ የታነጽን ከሆንን እንደ አካል ደግሞ እየተገነባን ሙሉ ሰው እንድንሆንለት የአገልግሎት ስራም እንዲበዛልን መልእክተኞችን ነቢያትን እረኞችን አስተማሪዎችን ከሰጠን ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ስጦታዎችን ከሰጠን እንደዚህ ያሉ ነገሮች ደግሞ የበዛላቸው አማኞች ከሆንን ከንግዲህ በማዕበል ወደ ፊትና ወደ ኋላ እየተነዳን በልዩ ልዩ አይነት የትምህርት ንፋስ በሰዎችም ረቂቅ ተንኮልና ማታለል ወዲያና ወዲህ እየተንገዋለልን ህጻናት መሆን አይገባንም።
ሳሚ ቱራ
ከሎሌ ወንጌላዊት ቤተክርስትያን YouTube ላይ የተወሰደ
https://www.youtube.com/