22/04/2026
"የአምላኬን ቤት አልተውም"
"የአምላካችንን ቤት ከቶ አንተውም" ነህ10:39
ክርስቲያን መሆን ማለት በአበባ በተጎዘጎዘ መንገድ ላይ መጓዝ ወይም ሁሉም ነገር የተመቻቸ አልጋ በአልጋ የሆነ ነው ማለት አይደለም። በተለይ በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ለታላቅ ዓላማ ስንነሳ፣ አገልግሎታችንን እንድናቆም፣ ተስፋ እንድንቆርጥና ከቤቱ እንድንርቅ የሚፈልጉ የውድቀት ተጠባባቂዎች በዙሪያችን ይበቅላሉ። ዛሬ የምንማረው እነዚህን ተግዳሮቶች አልፎ፣ ልብን በእግዚአብሔር አበርትቶ እስከ ፍጻሜው ስለመጽናት ነው።
1. ከድንጋይ የከበደው አንደበት
ጥንት ሰዎችን በድንጋይ ይወግሩ ነበር፤ ዛሬ ግን ወገራው መልክ ቀይሯል። ዛሬ የሚወገረው በድንጋይ ሳይሆን በአሉባልታ፣ በንቀት፣ በማሸማቀቅና በሐሜት በአሰመሳዮች ነው።
አንዳንድ ምሳሌዎችን እንመልከት
🗣ታላቅ ሥራ ለመሥራት ስትነሳ መጀመሪያ ከሚገጥምህ ተግዳሮት አንዱ “የምላስ ጦር” ነው።
1. ነህምያ (የውጭ ትችትና የአሽሙር ጦር ገጥሞት ነበር)
ነህምያ የኢየሩሳሌምን ቅጥር ለመገንባት ሲነሳ፣ ጠላቶቹ ሰንባላጥና ጦቢያ የድንጋይ ውርወራ ሳይሆን የቃላት ውርወራ ነበር የጀመሩት።
አሽሙሩ፦ “የሚገነቡትን ቅጥር ቀበሮ ቢወጣበት የድንጋዩን ግንብ ያፈርሰዋል” አሉት (ነህምያ 4:3)። ማለትም “ሥራችሁ ደካማ ነው ዋጋ የለውም” ብለው አፌዙበት።
ተግዳሮቱ፦ ወሬው የአይሁድን ልብ እንዲዝልና “አንችልም” እንዲሉ ለማድረግ የታቀደ ነበር።
ነገር ግን ነህምያ ለአሽሙራቸው መልስ አልሰጠም ከቁብ ሳይቆጥረው። ይልቁንም “እኔ ታላቅ ሥራ እሰራለሁ ፣ ወደ እናንተ መውረድ አልችልም” በማለት በትኩረት ሥራውን ቀጠለ።
2. ከትዳር አጋር፦ ሜልኮል (የዳዊት የቅርብ ሰው ነች )
አንዳንድ ጊዜ የከበደው ትችት የሚመጣው ከሩቅ ጠላት ሳይሆን አብሮ ካለ የቅርብ ሰው ነው። ንጉሥ ዳዊት የእግዚአብሔር ታቦት ሲገባ በደስታ በጌታ ፊት ሲዘል፣ ሚስቱ ሜልኮል በንቀት ተመለከተችው።
፦ “የእስራኤል ንጉሥ ዛሬ እንዴት የተከበረ!” በማለት በአሽሙር ተሳደበችው (2 ሳሙኤል 6:20)። ክብሩን ዝቅ ለማድረግና እንዳያመልክ ለማሸማቀቅ ሞከረች።
ዳዊት ግን “ከእግዚአብሔር ፊት ገና ዝቅ ወይም የተናቅሁ እሆናለሁ በአይንሽም እዋረዳለሁ... ” በማለት ለሰው ሳይሆን ለእግዚአብሔር እንደሚኖር አረጋገጠ። የሰው ንቀት ለእግዚአብሔርን ያለንን ክብር እና የቅንነት አገልግሎት እንዳይጋርድብን ዳዊት ምሳሌያችን ነው።
3. ከታዋቂ ግለሰቦች፦ ዊልያም ኬሪ (William Carey)
የዘመናዊ ሚስዮናውያን አባት የሚባለው ዊልያም ኬሪ ወደ ሕንድ ሄዶ ወንጌልን ለመስበክ ሲነሳ፣ የገጠመው ከአብያተ ክርስቲያናት መሪዎች ጭምር የነበረ ትችት ነው።
በአንድ ስብሰባ ላይ ስለ ወንጌል ተልዕኮ ሲናገር፣ አንዱ መሪ ተነስቶ “ወጣት፣ ተቀመጥ! እግዚአብሔር አረማውያንን መለወጥ ከፈለገ አንተንም እኛንም ሳይጠይቅ ያደርገዋል” በማለት አሸማቀቀው።
🗣ኬሪ ግን በዚህ የንቀት ቃል አልቆመም። "ታላቅ ነገርን ከእግዚአብሔር ጠብቅ፣ ታላቅ ነገርን ለእግዚአብሔር አድርግ" በሚለው መርህ ሕንድ ሄዶ መጽሐፍ ቅዱስን በብዙ ቋንቋዎች ተረጎመ።
4. ዳዊትና ወንድሙ ኤልያብ
ዳዊት ጎልያድን ሊጋጠም ወደ ሰልፍ ቦታው ሲመጣ፣ ትልቁ ወንድሙ ኤልያብ በንዴት ተቆጣው።
ዳዊትና ኤልያብ፦ የቅርብ ሰዎች ንቀትና ስም የማጥፋት ዘመቻ
(1 ሳሙኤል 17:28-30)
ዳዊት ጎልያድን ለመውጋት በቆራጥነት ሲነሳ፣ የመጀመሪያው እንቅፋት የሆነው የገዛ ወንድሙ ኤልያብ ነው። ኤልያብ ዳዊትን ለመግታት የተጠቀመባቸው ቃላት፦
ኃላፊነት የጎደለው ነህ፦ “እነዚያን ጥቂቶች በጎች በማን ዘንድ ተውሃቸው?” (አነስተኛ ግምት መስጠት)።
ትዕቢተኛ ነህ፦ “ኩራትህንና የልብህን ክፋት እኔ አውቃለሁ” (ያልሆነ ስም መለጠፍ)።
✍️ትልቅ ራዕይ ይዘህ ስትነሳ የቅርብ ሰዎችህ “ምን አቅም አለህ?” ወይም “ለዝና ብለህ ነው” ሊሉህ ይችላሉ። ዳዊት ግን ለወንድሙ መልስ በመስጠት ጊዜውን አላጠፋም፤ “ፊቱን ወደ ሌላ ሰው አዞረ” ይላል። ዛሬም አንተን ለሚያሸማቅቁህ ሰዎች መስጠት ያለብህ ትልቁ ምላሽ ትኩረት አለመስጠት ነው።
ዳዊት አንዳች በቃሉ ሳይናገር እልፎ ብሎ ፊቱን ወደ ሌላ ሰው አዞረ። ከሚተቹን ሰዎች ጋር መጨቃጨቅ ጊዜን መግደል ነው፤ ፊትን ወደ አላማ ማዞር ግን አዋቂነት ነው።
2. ነህምያና ጠላቶቹ፦ አሽሙርና የስነ-ልቦና ጦርነት
(ነህምያ 4:1-4)
ነህምያ የፈረሰውን ቅጥር ለመሥራት ሲነሳ ሰንባላጥና ጦቢያ በሦስት ደረጃ የተከፈለ የምላስ ውርወራ አደረጉበት፦
🗣ማንቆለጳሰስ (Belittling)፦ “እነዚህ ደካሞች አይሁድ ምን ያደርጋሉ?”
🗣ተስፋ ማስቆረጥ፦ “በአንድ ቀን ይጨርሳሉን?”
🗣ማሾፍ (Mockery)፦ “ቀበሮ ቢወጣበት ግንቡን ያፈርሰዋል”።
✍️ ጠላቶችህ በአገልግሎትህ ላይ “ቀበሮ ቢወጣበት ይፈርሳል” ይሉ ይሆናል። ስራህን እንደ ቀላልና እንደ ደካማ ይቆጥሩታል። ነህምያ ግን “አምላካችን ሆይ፥ ተንቀናልና ስማ” ብሎ ወደ ጸሎት ሄደ። በሰዎች አሽሙር ስትገፋ፣ ፊትህን ወደ ሰማይ መልስ እንጂ አካፋህን አትጣል።
3. ኢያሱና ካሌብ፦ የብዙኃኑ አሉባልታና ተቃውሞ
(ዘኁልቁ 14:1-10)
እነዚህ ሁለት ሰዎች “እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ነውና ምድሪቱን እንውረሳለን” ብለው በእምነት ሲናገሩ፣ መላው ማህበር ምን ለማድረግ እንደሞከረ አስተውሉ። “ማህበሩ ሁሉ በድንጋይ ሊወግሯቸው ተናገሩ” ይላል።
አብዛኛው ሰው በክፋት ሲተማማና አንተ ብቻህን በእምነት ስትቆም፣ የብዙኃኑ ድምፅ ሊያሸማቅቅህ ይችላል።
፦ በአገልግሎትህ ውስጥ ብዙ ሰዎች ቢቃወሙህም፣ አንተ ግን በእውነት ላይ ቁም፤ በዚያ ሰዓት “የእግዚአብሔር ክብር በደመና ተገለጠ” ይላል። ሰዎችን ለመምሰል ብለን አቋማህን አትቀይር፤ የእግዚአብሔር ክብር በአንተ ላይ የሚገለጠው በብቸኝነት ለእውነት ስትቆም ነው።
🗣እነዚህ ምሳሌዎች የሚያሳዩት አንድ እውነት አለ፦ "ድንጋይ የሚወረወረው ፍሬ ባለው ዛፍ ላይ ብቻ ነው።" ማንም የማይተችህ ከሆነ፣ ምናልባት ሰይጣን የሚፈራው ሥራ እየሠራህ ላይሆን ይችላል። ትችት የአገልግሎትህ “ባጅ” (Badge) እንደሆነ ቁጠረው።
1. ዳዊትና የእግዚአብሔር ጋሻነት
ጠላት በዙሪያችን ሲከብ፣ የሚያጽናናን ሰው ሲጠፋና የቅርብ የምንላቸው ሰዎች እንኳ ሊወግሩን ሲነሱ የምናገኘው ብርታት ከአምላካችን ነው።
ዳዊት በጺቅላግ ህዝቡ ሊወግሩት ሲሉ "ልቡን በአምላኩ በእግዚአብሔር አበረታ" (1 ሳሙኤል 30:6)።
እግዚአብሔር ለአብርሃም "እኔ ላንተ ጋሻህ ነኝ" አለው (ዘፍጥረት 15:1)። ጋሻ ከጠላት የሚሰነዘርን ፍላጻ እንደሚመክት ሁሉ፣ እግዚአብሔርም ከሚዘንብብህ ስነ-ልቦናዊና አካላዊ ጥቃት ይጠብቅሃል።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሊወግሩት ድንጋይ አነሱ፤ እርሱ ግን ከመካከላቸው አልፎ ሄደ (ዮሐንስ 8:59)።
ሰዎች በወሬና በንቀት ሊወግሩህ ሲሉ፣ ልክ እንደ ጌታህ "አልፈህ ሂድ"። ለሚሰነዘርብህ አሉባልታ ሁሉ ምላሽ መስጠት የለብህም፤ ዝምታና ወደ ፊት መራመድ ከሁሉ በላይ ትልቅ ምላሽ ነው።
🗣ስትወደድ የሚጠላህ፣ ስትወድቅ ደስ የሚለው "አስመሳይ ማህበር" ቢበዛም፣ አንተ ግን በሰው ሳይሆን በጋሻህ በእግዚአብሔር ተመካ።
3. ፈውስ በመገረፉ ቁስል ይሆንልሀል
ሰዎች በአንደበታቸው ሲገርፉህና ልብህን ሲያቆስሉት፣ ፈውሱ የሚገኘው በቆሰለው ጌታ ዘንድ ነው።
"እርሱም ስለ መተላለፋችን ቆሰለ... በእርሱም ቁስል እኛ ተፈወስን" (ኢሳይያስ 53:5)።
ሰዎች ካቆሰሉህ፣ ጌታ በቁስሉ ይፈውስሃል። ሰዎች ቢተዉህም፣ እርሱ ግን "አልተውህም ከቶም አልጥልህም" ብሎሃል።
4. የዘመናችንን ተግዳሮት ማሸነፊያ መንገዶች
ይህንን ሩጫ በድል ለመጨረስ የሚከተሉትን አራት ነጥቦች እንደ መጠቀም አስፈላጊ ነው፦
🗣ጸሎትና ህብረትን አለማቋረጥ፦ 🗣መነጠል ለጥቃት ያጋልጣል። 🗣በቤቱ ጸንተህ ተገኝ።
🗣በሉዓላዊነቱ መጽናት ይሁንልህ፦ 🗣"ሁሉን የሚገዛው ጌታ ከእኔ ጋር ነው" ብለህ እመን።
🗣ቅንነትን አትጣ፦ ሰዎች ክፉ ስለሆኑ አንተ ክፉ አትሁን። የልብ ቅንነት በረከትን የመጣል የቅኖች ትውልድ ይባረካል።
🗣ጌታን እያዩ መሮጥ "የእምነታችንን ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን በመመልከት..." (ዕብራውያን 12:2)። ትኩረትህ አገልግሎቱ ላይ እንጂ አገልጋዩ ላይ አይሁን።
🗣እነዚህ ሁሉ ሰዎች ቢሰሙአቸው ኖሮ ዛሬ ታሪካቸው አይጻፍም ነበር።
✍️ዳዊት ወንድሙን ቢሰማ ጎልያድን አይጥልም ነበር።
✍️ነህምያ አሽሙሩን ቢያዳምጥ የኢየሩሳሌም ቅጥር አይታደስም ነበር።
✍️ኢያሱና ካሌብ ድንጋዩን ቢፈሩ ርስታቸውን አይወርሱም ነበር።
በመጨረሻም
የተጠራህበት ዓላማ ከሰዎች ወሬ ይበልጣል። "የአምላኬን ቤት አልተውም" ስንል፣ ለሰዎች ብለን ሳይሆን ለጠራን ጌታ ታማኝ ሆነን መቆማችንን እያወጅን ነው።
ዛሬ ላንተ የሚመጣው የምላስ ጦር የአገልግሎትህ መጀመሪያ እንጂ መጨረሻ አይደለም። ጋሻህ እግዚአብሔር ነውና “የአምላኬን ቤት አልተውም” ብለህ ሩጫህን ቀጥል!
🗣 ድንጋይ የሚወረውሩ ሁሉ ያልፋሉ፤ የእግዚአብሔር ቃል እና አማኞቹ በክርስቶስ ለዘለዓለም እንኖራለን።
ፓ/ር ኤርምያስ ጌታቸው