19/12/2025
የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶች ፌዴሬሽን የንቅናቄ ኮንፍረንስ አካሄደ።
ታህሳስ 9 ቀን 2018 ዓ/ም ወጣቶች እና ስፖርት ቢሮ
የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶች ፌዴሬሽን በጎ ፈቃድ ለማሕበረሰብ ለውጥ፤ የወጣቶች ሚና ለሁለንተናዊ ብልጽግና በሚል መሪ ቃል የንቅናቄ ኮንፍረንሱን አካሂዷል።
በኮንፈረንሱ መክፈቻ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የአዲስ አበባ ከተማ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ማዕከል ም/ሀላፊ እና የፖለቲካ አቅም ግንባታ ሀላፊ ወ/ሮ አለም ፀሀይ ሽፈራው ፌዴሬሽኑ ለከተማዋ ብሎም ለሀገር ሁለንተናዊ እድገት ዘርፈ ብዙ ስራዎችን እየሰራ መሆኑን ገልፀው በቀጣይ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ አሳስበዋል።
ወጣቶች በሀገራቸው ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ ቀጥተኛ ተሳታፊ በመሆን በኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ ላይ ደማቅ አሻራቸውን በማስቀመጥ እዳን ሳይሆን ምንዳን ለቀጣዩ ትውልድ ማስተላለፍ እንደሚገባ ወ/ሮ አለምፀሀይ ገልፀዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ሀላፊ አቶ በላይ ደጀን የአዲስ አበባ ወጣቶች ፌዴሬሽን ከተመሰረተበት ጊዜ አንስቶ የከተማውን ወጣቶች ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ተሳታፊነት እና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የበኩሉን አስተዋፅኦ እየተወጣ እንደሚገኝ ገልፀዋል።
ፌዴሬሽኑ በቀጣይ አደረጃጀቱን እና የሚሰራቸውን ስራዎች አጠናክሮ በማስቀጠል ለከተማዋ ሁለንተናዊ ልማት እና ሰላም መረጋገጥ ፋና ወጊ መሆን እንዳለበት አቶ በላይ አሳስበዋል።
የአዲስ አበባ ወጣቶች ፌደሬሽን ፕሬዘዳንት ወጣት ገዛኸኝ ወልደማርያም ፌዴሬሽኑ የበጎ ፈቃድ ስራዎችን ጨምሮ ለከተማዋ ሁለንተናዊ እድገት እያበረከተ ያለውን አስተዋጽኦ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል።
ወጣቶች በሀገር መንግስት ግንባታ ላይ ከፍተኛ ድርሻ እንደነበራቸው ወጣት ገዛኸኝ አስታውሰው የመንግስትን የልማት እና የሰላም ግቦችን ለማሳካት ከመቸውም ጊዜ በላይ ፌዴሬሽኑ እንደሚሰራ አሳውቀዋል።
በንቅናቄ ኮንፈረሱ ላይ የከተማው ከፍተኛ አመራሮችና የፌዴሬሽኑ አባላት ተሳትፈውበታል።