16/03/2026
👇👇👇👇👇
የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሩአችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ፥ የኑሮአቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነታቸው ምሰሉአቸው።”
— ዕብራውያን 13፥7
ከሕይወት ግርግር፣ ከትግሉ መሃል፣ ከሩጫውም ድካም አፍታ እንውሰድና ቁጭ እንበል፤ ማንም ከአቅሙ በላይ እንዳልተፈተነ ለማወቅ እንጠይቅ፣ በአባቶቻችን ትናንት አዲስ የመሰለንን የኛን ዛሬ እንመዝነው፣ ነጋችንንም እንተልም ብለን ታህሳስ 5 በእለተ ሰንበቱ እኛ የአልባስጥሮስ አካላት በጋሽ ሽፈራው ወ/ሚካኤልና በወ/ሮ ሰብለ ቤት ለመገኘት ተቃጥረናል ።
ቀኑ የወሩ የመጀመርያ እሁድ እንደመሆኑ ብዙሀኑ የአልባስጥሮስ ቤተሰብ የጌታን ሞትና ትንሳኤ ለማሰብ በጠዋት ቤተክርስቲያን ከትሟል።የጌታ እራት መርሀግብር እንደተጠናቀቀ አልባስጥሮሳውያን በጋራ ጥሩ የማዕድ መቁረስ ስነስርሀት አካሂደናል(ምሳ መሆኑ ነው እንግዲህ )። የቀሩትም የአልባስጥሮስ አካላት ያለወትሯቸው ጉዞ ለማድረግ ከተቀጣጠርንበት ሰሀት ቀደም ብለው በጌጃ ቃለህይወት ቤተክርስቲያን ቅጥር ግቢ ውስጥ ተገኝተውዋል። ከጥቂት መጠባበቅ በኋላ በ2025 ሞዴል German ስሪት "ታታ ቅጥቅጥ" መኪና ሀያት ወደሚገኘው የጋሽ ሽፈራው እና የወይዘሮ ሰብለ መኖርያ ቤት አቀናን። ገና ከበር መደነቃችን "ሀ" ብሎ ጀመረ። የተንጣለለው መኖርያ ግቢያቸው ከሞገሳሙ ዛፍ ጋር ተዳምሮ ላየው ሰው መደነቅን እና የልብ መረጋጋትን የመፍጠር ልዩ ሀይል አለው። በትልቁ ግቢያቸው እንደ ትልቅ እንግዳ በአክብሮት እና በደስተኛነት ተቀበሉን። ቤተሰቡን ተዋወቅን። ወ/ሮ ሰብለ ''ለካ እግዚአብሔር ብዙ ልጆች ሰጥቶኛል'' በማለት ደስ መሰኘታቸውን ገልፀውልን፤ "አኛ" እግዚአብሔር እነዚህን የእምነት አባትና እናቶች ለቤተክርስቲያን ስለሰጠ ፤ "እነርሱም" እግዚአብሔር እኛን ለቤተክርስቲያን ስለሰጠ ለማመስገን በጸሎት የእለቱን መርሀግብራችንን ጀመርን። አምልኮ ተከተለ፣ ከዚያም ሁላችንም በጉጉት ስንጠብቀው ወደነበረው የጋሽ ሽፈራው እና የወ/ሮ ሰብለ የህይወት ተሞክሮ አመራን።
''እኛ ቤት ድህነትና ፍቅር በሽ በሽ ነበሩ'' አሉ የቤቱ አራተኛ ልጅ የሆኑት ጋሽ ሽፈራው ስለ አስተዳደጋቸው ሲነግሩን። ጊዜ ለማሳለፍ ወደ ሚሲዮናውያን ማዕከል ከጓደኛዬ ጋር በሄድኩበት ቀን ነበር ከሮሜ 3:23 እና ሮሜ 6:23 ለመጀመሪያ ጊዜ የወንጌልን ቃል የሰማሁት። ወደ ጌጃ ቃለህይወት ቤተክርስቲያን የመጣሁትም ጥቁር አንበሳ አካባቢ በሚገኘው በSIM በኩል ነበር በማለት ጋሽ ሽፈራው ወደ ጌታ የመጡበትን እና አገልግሎት የጀመሩበትን መንገድ አጋርተውናል። ጋሽ ሽፈራው በመሪነት የአገልግሎት ዘመናቸው ለጌጃ ቃለህይወት ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ምሳሌ መሆን የሚችል ብዙ ትልልቅ ስራዎችን የሰሩ አባት ናቸው።
በዕለቱ በአገልግሎት፣ በህብረት፣ በቅድስናና በባለራዕይነት ዙርያ ምልከታቸውን አጋርተውናል። በፍጥነት እና በጩኸት በተሞላ በዚህ ጠማማ ትውልድ ውስጥ አንደ ''እግዚያብሔር ቃል'' ያለ አስተማማኝ ድምፅ፣ ደካማ ሀይለኛ እንደሚሆንበት ''ፀሎት''፣ ህይወትን ከመጨረሻ ለመጀመር እንደሚያስችል ''ዓላማ'' ያለ ሁነኛ መሳርያ በዚህ ዘመን ላለ ወጣት እንደሌለ ተምረናል። ከተናገሩት ብቻ ሳይሆን ከኖሩት ለጥያቄዎቻችን ብዙ ምላሾችን አግኝተናል። በውይይታችን መሀል የፍቅራቸውን መቀባበል፤ ጨዋታ አዋቂተታቸውን፤ መከባበራቸውን አይተናል። ለአክብሮታችን መግለጫ ይሆን ዘንድ ጋቢ አልብሰናል።
በመጨረሻም ጋሽ ሽፈራው እስከ በር ሸኝተውን ፤ ኮፍያቸውን አውልቀው ሲሰናበቱን በትንሻ ልባችን ውስጥ ትልቅ ፍቅር ተክለዋል ። በዚህ ሁሉ ውስጥ ጋሽ ሽፈሪው እንዲሁም ባለቤታቸው ወ/ሮ ሰብለ ያሳዩን ፍቅርና አክብሮት መቼም ከልባችን አይጠፋም። ከጉብኝታችን ተበረታተን፣ አስተውለን እና አመስግነን ተመልሰናል። የትውልድ የወደፊት ዕጣ ፈንታ ከእኛ በፊት የነበሩትን በጥንቃቄ በማዳመጥ እንደሚጠናከር ተረድተናል።
ታህሳስ 5 ቀን 2018 ዓ.ም
አልባስጥሮስ ህብረት
Geja Kale Hiwot Church
Geja Kale Hiwot Church, Youth for Christ