የኢትዮጵያ ሙስሊሞች መብት ተሟጋች ድርጅት/ /Ethiopian muslim rights gaurd

  • Home
  • Ethiopia
  • Addis Ababa
  • የኢትዮጵያ ሙስሊሞች መብት ተሟጋች ድርጅት/ /Ethiopian muslim rights gaurd

የኢትዮጵያ ሙስሊሞች መብት ተሟጋች ድርጅት/ /Ethiopian muslim rights gaurd Contact information, map and directions, contact form, opening hours, services, ratings, photos, videos and announcements from የኢትዮጵያ ሙስሊሞች መብት ተሟጋች ድርጅት/ /Ethiopian muslim rights gaurd, Non-Governmental Organization (NGO), Addis Ababa.

26/04/2026

ሳውዲ አረቢያ ከኢራን ጋር የሚደረገውን ድርድር ለማስቀጠል ሲባል በአሜሪካ በኩል በእስራኤል እና ሊባኖስ መካከል የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረግ ግፊት ማድረጓ ተገለጸ

በሊባኖስ የተኩስ አቁም ከመታወጁ አንድ ቀን ቀደም ብሎ በትራምፕ እና በልዑል መሀመድ ቢን ሰልማን መካከል የግል ስልክ ንግግር ተካሂዷል።

ሳውዲ አረቢያ ከኢራን ጋር የሚደረገውን ንግግር ለማስቀጠል አሜሪካ በሊባኖስ የተኩስ አቁም ለማምጣት ቅድሚያ እንዲሰጥ ግፊት ማድረጓን በርካታ የአሜሪካ፣ የምዕራባውያን እና የአረብ ባለስልጣናት ለ“ሚድል ኢስት አይ” ገልጸዋል። ይህ የሆነው ግዛቱ የሆርሙዝ ስርጥን እንደገና ለማስከፈት ድርድር እየተደረገ ባለበት ወቅት ነው።

የሳውዲ አረቢያው አልጋ ወራሽ ልዑል መሀመድ ቢን ሰልማን ባለፈው ረቡዕ በነበረው የግል ስልክ ንግግር በሊባኖስ የተኩስ አቁም ማድረግ ስላለው አስፈላጊነት ለፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ያሳሰቡ ሲሆን፣ ትራምፕ ሐሙስ ዕለት ያወጁት የ10 ቀን የተኩስ አቁም በዚሁ የሳውዲ አረቢያ ግፊት የመጣ መሆኑ ተነግሯል።

ይሁን እንጂ እስራኤል ለስምምነቱ ተገዢ መሆኗ እና ትራምፕ በኔታንያሁ ላይ የሚኖራቸው የጫና መጠን እስካሁን ግልጽ አይደለም። በሌላ በኩል ሄዝቦላህ የሊባኖስ መንግስት ከእስራኤል ጋር ቀጥተኛ ንግግር በማድረጉ ተቃውሞውን ገልጿል።

26/04/2026

ሂዝቦላህ በእስራኤል እና በሊባኖስ መካከል የተደረሰውን የተኩስ አቁም ስምምነት አስመልክቶ በሰጠው አስተያየት፤ ሁኔታዎች ከመጋቢት 2 በፊት ወደነበሩበት መመለስ አለባቸው ብሏል።

የሂዝቦላህ የፕሬስ ቢሮ ባወጣው መግለጫ፦ "የተኩስ አቁሙ በሁሉም የሊባኖስ ግዛቶች ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶችን ሙሉ በሙሉ ማቆምን ማካተት አለበት፤ ለእስራኤል ኃይሎች ምንም ዓይነት የነፃ እንቅስቃሴ መፍቀድ የለበትም፣ እንዲሁም ሁኔታዎች ከመጋቢት 2 በፊት ወደነበሩበት መመለስ አለባቸው" ብሏል።

26/04/2026

ሰሜን ኮሪያ ዛሬ ሰኞ Hwasongpho-11 Ra የተሰኙ አምስት የአጭር ርቀት ተወንጫፊ ታክቲካል ባለስቲክ ሚሳይሎችን መተኮሷን በይፋ አስታውቃለች

ይህ የሰሜን ኮሪያ ይፋዊ መግለጫ የወጣው ደቡብ ኮሪያ እና ጃፓን ወደ ምሥራቅ ባሕር (የጃፓን ባሕር) የተተኮሱ ሚሳይሎችን መመልከታቸውን ካሳወቁ በኋላ ነው።

26/04/2026

በእየሩሳሌም የሚገኘው የዕብራይስጥ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች ያካሄዱት አዲስ ጥናት እንደሚያመለክተው፤ ከኢራን ጋር እየተካሄደ ባለው ጦርነት ምክንያት በእስራኤላውያን የጤና ሁኔታና ተያያዥ ባህሪያት ላይ ጉልህ የሆኑ አሉታዊ ተጽዕኖዎች ታይተዋል።

ይህ ጥናት በዋነኝነት ትኩረት ያደረገው ግጭቱ በሰዎች የዕለት ተዕለት የአኗኗር ዘይቤ ላይ በሚያሳድረው ጫና ሲሆን፣ በተለይም የሥነ-ልቦና ውጥረትና ጭንቀት መጨመር ለጤና ጠንቅ የሆኑ ልማዶች እንዲስፋፉ ምክንያት መሆኑን ያመላክታል።

በዚህም መሠረት የጥናቱ ውጤት እንደሚያሳየው፣ በጦርነቱ ሳቢያ በብዙዎች ዘንድ የተመጣጠነ ምግብ አጠቃቀም መቀነስ፣ የአካል ብቃት እንቅስቃሴን ማቆም እንዲሁም የእንቅልፍ መዛባት ችግሮች በስፋት ተስተውለዋል። ይህም በረጅም ጊዜ ሂደት በሕዝብ ጤና ላይ ከፍተኛ መዘዝ ሊያስከትል እንደሚችል ተመራማሪዎቹ አስገንዝበዋል።

MFM - ለማህበረሰብ ፍትህ

ለተጨማሪ መረጃ በቴሌግራም ይከተሉን

📲 ቴሌግራም: https://t.me/mekaneselamfm

26/04/2026

የኢራን ማዕከላዊ ዕዝ ኸተሙል አንቢያ ፤ ሀገሪቱ "ባላንጣ" ካለችው አካል ለሚሰነዘር ማንኛውም የቃል ኪዳን ጥሰት ወታደራዊ ኃይሏ ጠንካራ ምላሽ ለመስጠት ዝግጁ መሆኑን ገለጸ።

ማክሰኞ ዕለት በኢራን መንግሥታዊው ቴሌቪዥን ይፋ የሆነው የማዕከላዊ ዕዙ መግለጫ የተኩስ አቁም ጥሰቶች እየተፈጸሙ መሆኑን እና ዕዙ ምላሽ ለመስጠት መዘጋጀቱን አስታውቋል።

ኢራን "ጠላት" ስትል የጠራችው አካል ግዴታዎቹን የማያከብር ከሆነ፤ የሀገሪቱ ወታደራዊ ኃይሎች ማዕከላዊ ዕዝ በንቃት እየተከታተለ መሆኑን እና እርምጃ ለመውሰድ ዝግጁ ነው ብሏል።

26/04/2026

የአሜሪካ የባህር ላይ እገዳ ዓለም አቀፋዊ መልክ መያዙ ተገለጸ

MFM | የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስትር ፔት ሄግሴት፣ አሜሪካ በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችው የባህር ላይ እገዳ አሁን ላይ ዓለም አቀፋዊ ገጽታ ማግኘቱን ይፋ አድርገዋል። ሚኒስትሩ ይህንን የተናገሩት፣ በኢራን የነዳጅ ንግድ ውስጥ ሚና አላቸው ተብለው የሚጠረጠሩ ሁለት የ"ጥቁር የባህር ኃይል" (Dark Fleet) መርከቦች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ተከትሎ ነው።

የመርከቦቹ በቁጥጥር ስር መዋል

ሚኒስትሩ እንደገለጹት፣ በቁጥጥር ስር የዋሉት መርከቦች አሜሪካ የጣለችው እገዳ በይፋ ከመተግበሩ ቀደም ብሎ ከኢራን ወደቦች የወጡ ነበሩ። መርከቦቹ የክትትል ስርዓታቸውን በማጥፋት እና ማንነታቸውን በመደበቅ በባህር ላይ ሲንቀሳቀሱ ቢቆዩም፣ በአሜሪካ እና በአጋር ሀገራት የተቀናጀ የክትትል መረብ አማካኝነት በቁጥጥር ስር ሊውሉ ችለዋል። ይህ እርምጃ አሜሪካ በኢራን የባህር ላይ ንግድ እንቅስቃሴ ላይ ያላትን የቁጥጥር አቅም እንደሚያሳይ ተንታኞች ይገልጻሉ።

የ"ጥቁር የባህር ኃይል" አሠራር

"ጥቁር የባህር ኃይል" ወይም "Dark Fleet" በመባል የሚታወቁት መርከቦች፣ ዓለም አቀፍ ማዕቀቦችን በመጣስ የኢራንን ድፍድፍ ነዳጅ በድብቅ ለማጓጓዝ የሚያገለግሉ ናቸው። እነዚህ መርከቦች የትራንስፖንደር መሣሪያዎቻቸውን በማጥፋት የጂፒኤስ ምልክታቸውን ይደብቃሉ፤ እንዲሁም በሌሎች ሀገራት ስም በመመዝገብ የአሜሪካን እገዳ ለማለፍ ይሞክራሉ። ሄግሴት ፣ አሜሪካ አሁን እነዚህን ድብቅ እንቅስቃሴዎች ለመለየት የሚያስችል ቴክኖሎጂ እና የዲፕሎማሲ ትብብር አጠናክራለች ብለዋል።

የእገዳው ዓላማና ቀጣናዊ አንድምታ

የአሜሪካ የባህር ላይ እገዳ ዋና ግብ ኢራን ወደ ውጭ የምትልከውን የነዳጅ ምርት በማገድ፣ ሀገሪቱ ለቀጣናዊ የታጠቁ ቡድኖች የምታደርገውን የገንዘብ ድጋፍ ማቋረጥ ነው። ሚኒስትሩ አፅንዖት እንደሰጡት፣ እገዳው ከኢራን የባህር ክልል አልፎ በዓለም አቀፍ የባህር መስመሮች ላይ በሙሉ ተግባራዊ ሆኗል። ይህም ኢራን በዓለም ገበያ ላይ ያላትን የነዳጅ ተፅዕኖ በመቀነስ፣ በመካከለኛው ምስራቅ ያለውን የጂኦ-ፖለቲካ ሚዛን ለመቀየር ያለመ ስልታዊ እርምጃ ተደርጎ ተወስዷል።

ቀጣይ ተፅዕኖ

ይህ የአሜሪካ እርምጃ በዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ ላይ ሊያመጣ የሚችለው መዋዥቅ በዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን በስፋት እየተወራ ነው። በተለይም መርከቦቹ ከመታገዳቸው በፊት ከኢራን መውጣታቸው፣ አሜሪካ በእገዳው ጊዜ ስር የሚወድቁ መርከቦችን ብቻ ሳይሆን፣ እገዳውን ለመሸሽ የሞከሩትንም ጭምር እንደምትከታተል የሚጠቁም ጠንካራ መልእክት ሆኗል።

26/04/2026

የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ፣ ከታህሳስ 2024 ወዲህ በተደረገላቸው መደበኛ የህክምና ምርመራ የፕሮስቴት ካንሰር እንደተገኘባቸው ዓርብ ዕለት ይፋ አድርገዋል

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት መግለጫ፣ ካንሰሩ በቅድመ ደረጃ ላይ በምርመራ መገኘቱን በመግለጽ፣ ከዚያ ጊዜ አንስቶ አስፈላጊውን የህክምና ክትትልና ህክምና ሲያደርጉ እንደቆዩ አስታውቀዋል። ይህን የጤና ሁኔታ አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ፣ ህክምናው ስኬታማ እንደነበር እና በአሁኑ ወቅት የጤንነት ሁኔታቸው የተረጋጋ መሆኑን በመጠቆም፣ ተግባራቸውን በመደበኛነት ለመቀጠል የሚያስችል ብቃት ላይ እንደሚገኙ አረጋግጠዋል።

ይህ የጤና መረጃ ይፋ የሆነው ኔታንያሁ በተለያዩ ውስብስብ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ጉዳይ ፖለቲካዊ ውጥረት ውስጥ ባሉበት ወቅት ነው። ሆኖም፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የጤና እክሉ በስራቸው ላይ ምንም አይነት ተጽዕኖ እንደሌለው በመግለጽ፣ በሀገሪቱ የፖለቲካ እና የደህንነት ጉዳዮች ላይ ሙሉ ትኩረታቸውን እንደቀጠሉ ለማስረዳት ሞክረዋል።

26/04/2026
26/04/2026

በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ያንዣበበው የጦርነት ደመና - የዲፕሎማሲው መክሸፍ እና የቴህራን "የባህር ላይ ከበባ" ስጋት

MFM |ልዩ ዘገባ Mohammed Miftah Derb

በመካከለኛው ምስራቅ ለ57 ተከታታይ ቀናት የቀጠለው የኢራን ጦርነት፣ አሁን ላይ ዓለምን ወደ ከፍተኛ ስጋት ያስገባ አዲስ ምዕራፍ ላይ ይገኛል። ለሳምንታት በፓኪስታን አደራዳሪነት ሲከናወን የነበረው የሰላም ጥረት፣ በፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ድንገተኛ ውሳኔ ሳቢያ በጨለማ ተውጧል። የቴህራን "በከበባ ውስጥ ሆኜ አልደራደርም" ባይነት እና የዋሽንግተን "ካርዶቹ ሁሉ በእጄ ናቸው" የሚለው ትዕቢት ቀጠናውን ወደማይታወቅ ጥፋት እየገፋው ይገኛል።

የሰላም ጥረቱ መክሸፍ፦ ከኢስላማባድ እስከ ዋይት ሀውስ

የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ በፓኪስታን በኩል ያቀረቡት የሰላም ማዕቀፍ፣ በዋሽንግተን ዘንድ "በቂ አይደለም" በሚል ውድቅ ተደርጓል። ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተወካዮቻቸውን እና ከፍተኛ አማካሪዎቻቸውን ወደ ኢስላማባድ ሊያደርጉት የነበረውን ጉዞ በድንገት መሰረዛቸው፣ አሜሪካ በዲፕሎማሲው መንገድ ያላትን ተስፋ መቁረጥ ያሳያል። ትራምፕ በ"ትሩዝ ሶሻል" ገጻቸው እንዳሰፈሩት፣ ኢራን ያቀረበችው ሀሳብ የአሜሪካን ጥቅም የማያስከብር በመሆኑ ጉዞው "የጊዜ ብክነት" ነው ብለዋል። ይህ ደግሞ ለቀናት ሲጠበቅ የነበረውን የተኩስ አቁም ተስፋ አሟጥጦታል።

"ሆርሙዝ ወሽመጥ " ከበባ እና የቴህራን ቁጣ

የኢራኑ ፕሬዝዳንት መስዑድ ፔዜሽኪያን ለፓኪስታኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ሸህባዝ ሸሪፍ በግልጽ እንደተናገሩት፣ ኢራን በአሜሪካ የባህር ኃይል በኩል የተጣለባትን የሆርሙዝ ወሽመጥ ከበባ እንደ "የጦርነት አዋጅ" ትቆጥረዋለች። ቴህራን "ሽጉጥ በጭንቅላቴ ላይ ተደግኖ ድርድር አልቀመጥም" በሚል አቋሟ መጽናቷ፣ በአካባቢው ያለውን ወታደራዊ ፍጥጫ ይበልጥ አክሮታል። በተለይም አዲሱ የበላይ መሪ ሙጅታባ ኾማኒ ስልጣን በያዙ ማግስት፣ ሀገሪቱ በደቡባዊ ኢራን በሚናብ ከተማ በትምህርት ቤት ላይ ደረሰ ለተባለው ጥቃት የአጸፋ እርምጃ የመውሰድ ዝግጅቷን እያጠናከረች እንደሆነ ይነገራል።

የእስራኤል ሚና እና የሊባኖስ ግንባር

ጦርነቱ በኢራን ምድር ብቻ ሳይወሰን በሊባኖስ ግንባርም ክፉኛ እየተፋፋመ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ "ሄዝቦላህ የሰላም ጥረቱን እያደናቀፈ ነው" በሚል በደቡባዊ ሊባኖስ ላይ የኃይል እርምጃ እንዲወሰድ ትዕዛዝ ማስተላለፋቸው፣ ጦርነቱ ክልላዊ ይዘቱን ይበልጥ እንዲያሰፋ አድርጎታል። ይህ ደግሞ ኢራን ከውጭ በሚደረግባባ ከበባ፣ ከውስጥ ደግሞ በመሪዎች ለውጥ እና በመሰረተ ልማት ውድመት ሳቢያ ለከፋ ቀውስ እንድትጋለጥ አድርጓታል።

የቀጣዩ ስልክ ጥሪ ጥበቃ

ምንም እንኳን ፕሬዝዳንት ትራምፕ "ኢራን መነጋገር ከፈለገች ስልኩን አንስታ መደወል ትችላለች" ቢሉም፣ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው የ"እምነት ማጣት" ግን ከመቼውም ጊዜ በላይ ሰፍቷል። ቴህራን ከበባው እንዲነሳላት ትጠይቃለች፤ ዋሽንግተን ደግሞ ኢራን ሙሉ በሙሉ እጅ እንድትሰጥ ትፈልጋለች። በዚህ መካከለኛ መስመር ላይ የተገኘው መፍትሄ ባለመኖሩ፣ መጪዎቹ ቀናት በመካከለኛው ምስራቅ የታሪክ ምዕራፍ ላይ የደም ጠብታ ሊያክሉ እንደሚችሉ ምልክቶች እየታዩ ነው።

26/04/2026

የአሜሪካ ሽንፈት - የ"ሥልጣኔ ፀሐይ" መጥለቅ ምልክቶች

MFM |ልዩ ዘገባ በ Mohammed Miftah Derb

አሜሪካ በኢራን ላይ የከፈተችው ጦርነት ወታደራዊ ድልን ሳይሆን፣ የልዕለ-ኃያልነት ማክተሚያን (The End of Unipolarity) እያበሰረ ይገኛል። ሽንፈቱ የሚለካው በወታደራዊ ጥፋት ብቻ ሳይሆን፣ አሜሪካ ዓለምን የምታዝበት "የስልክ ጥሪ" ጡንቻ መላላቱ ጭምር ነው።

አሜሪካ የኢራንን የኑክሌር ተቋማት ለማውደም ብትሞክርም፣ የኢራን "አይገመቴ" (Asymmetric) የመከላከል አቅም ጥቃቱን ከከፊል ስኬት በላይ እንዳይሆን አግዶታል። ለብዙ ዓመታት ማዕቀብ እና የዶላር የበላይነት እንደ ፖለቲካዊ ጅራፍ ሲያገለግሉ ቆይተዋል። አሁን ግን ኢራን በማዕቀብ ውስጥ ሆና የገነባችው የውስጥ አቅም እና ከምስራቁ ዓለም (ከቻይና እና ከሩሲያ) ጋር የፈጠረችው ትስስር አሜሪካን "ተፅዕኖ አልባ" አድርጓታል። የዩናይትድ ስቴትስ የቅርብ አጋሮች (ሳውዲ አረቢያ እና ዩኤኢ) አሜሪካ ሙሉ ጥበቃ ልታደርግላቸው እንደማትችል በመረዳታቸው፣ ፊታቸውን ወደ ቴህራን እና ቤጂንግ ማዞራቸው የዋሽንግተን ትልቁ ዲፕሎማሲያዊ ሽንፈት ነው።

የታሪክ ምጸት - የኢራን ጦርነት እና የ1956ቱ የስዊዝ ቀውስ መመሳሰል

እ.ኤ.አ. በ1956 ብሪታንያ ግብፅን በወረረችበት ወቅት፣ በአሜሪካ "የአንድ ስልክ ጥሪ" እና በፓውንድ ላይ በተሰነዘረ የኢኮኖሚ ዛቻ ልዕለ-ኃያልነቷን አጥታለች። ዛሬ ታሪክ ራሱን እየደገመ ነው። በ1956 ብሪታንያ መሪነቱን ለአሜሪካ እንዳስረከበች ሁሉ፣ በ2026 አሜሪካ በኢራን ረግረግ ውስጥ መዘፈቋ መሪነቱን ለዩራሺያ ኃይሎች (ቻይና፣ ሩሲያ እና ኢራን) እያስረከበች መሆኑን ያሳያል።

አሜሪካ በወቅቱ ፓውንድን "ውዳቂ ወረቀት አደርገዋለሁ" እንዳለችው ሁሉ፣ ዛሬ ዓለም ዶላርን በመሸሽ (De-dollarization) ዶላርን ወደ ተራ ወረቀትነት እየቀየረው ነው። ይህ "የአሜሪካ ስዊዝ ቅጽበት" (Suez Moment) የታሪክ ምስልስሎሽ ነው።

የፔትሮ-ዶላር ውድቀት እና የ1925ቱ የፓውንድ ስህተት

የብሪታንያ ውድቀት የጀመረው በ1925 ፓውንድን ከወርቅ ጋር ለማያያዝ በተሞከረ የተሳሳተ የፋይናንስ ውሳኔ ነበር። አሜሪካም ዛሬ ተመሳሳይ ስህተት እየደገመች ነው። አሜሪካ ዶላርን በፖለቲካዊ ጠላቶቿ ላይ እንደ መሣሪያ ስትጠቀም፣ ዓለም አማራጭ መፈለግ ጀምሯል። የሳውዲ አረቢያ ከፔትሮ-ዶላር ሥርዓት መውጣት ስጋት፣ የዶላርን ዓለም አቀፍ የበላይነት የሚንድ "የመጨረሻው ምዕራፍ " ነው። ልክ ዩናይትድ ስቴትስ የብሪታንያን ዱካ ተከትላ እንደተነሳች ሁሉ፣ ዛሬ የብሪክስ (BRICS) ሀገራት የራሳቸውን የመገበያያ ሥርዓት በመፍጠር የአሜሪካን የገንዘብ የበላይነት ሰባብረውታል።

የትራምፕ ፖለቲካዊ ብስለት ማነስ እና የኔታንያሁ "የማይቀለበስ" ዕቅድ

የአሜሪካ የውስጥ ፖለቲካ መከፋፈል ለውድቀቷ ትልቅ ምክንያት ሆኗል። የፕሬዝዳንት ትራምፕ "አሜሪካ ትቅደም" (America First) ፖሊሲ የቆዩ ጥምረቶችን (እንደ ኔቶ ያሉ) አዳክሟል። ዲፕሎማሲያዊ ፕሮቶኮሎችን አለማክበር እና ዓለም አቀፍ ስምምነቶችን ማፍረስ የአሜሪካን "Soft Power" (የሥነ-ልቦና የበላይነት) አጥፍቶታል።

የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታንያሁ የኢራንን ወታደራዊ መዋቅር ለመበጣጠስ ያላቸው "የማይቀለበስ ዕቅድ" አሜሪካን ወደማትወጣው ቀጠናዊ ጦርነት ጎትቷታል። ይህ ደግሞ አሜሪካን ከሥነ-ምግባር እና ከኢኮኖሚ አቅም በላይ የሆነ ሸክም ጭኖባታል።

የኢራን አስደናቂ አቅም እና የ"መልቲ-ፖላር" ዓለም ልዕለ-ኃያልነት

ኢራን አፍጋኒስታን ወይም ኢራቅ አይደለችም። ያላት ወታደራዊ እና ጂኦ-ፖለቲካዊ ክብደት አሜሪካን እጅ እንድትሰጥ አድርጓታል። ኢራን ቢሊዮን ዶላር የሚያወጡ የአሜሪካ የጦር መሣሪያዎችን በጥቂት ሺህ ዶላር በሚገመቱ ድሮኖች እና ሚሳይሎች የማምከን አቅም አሳይታለች። ጦርነቱን በማስረዘም "በረጅም ጦርነት ማሸነፍ" (Winning by surviving) የሚለውን ስልት በሚገባ ተጠቅማበታለች። ዛሬ ዓለም ወደ "ባለብዙ ዋልታ" (Multipolar) ሥርዓት ተሸጋግላለች። ቻይና በኢኮኖሚ፣ ሩሲያ በወታደራዊ እና ኢራን በቀጠናዊ ተፅዕኖ የተሳሰሩበት "የዩራሺያ ጥምረት" የአሜሪካን ብቸኛ ልዕለ-ኃያልነት ቀብሮታል።

26/04/2026

የብሪታንያ ኢምፓየር ውድቀት እና የስዊዝ ቀውስ - ታሪክ ራሱን ሲደግም

MFM |ልዩ ዘገባ በ Mohammed Miftah Derb

በህዳር 1956 እ.ኤ.አ. በታሪክ የዓለምን ፖለቲካዊ መልክ ለዘላለም የለወጠ ክስተት ተፈጠረ። ይህ ክስተት ፀሐይ የማትጠልቅበት ኢምፓየር ወደ አንድ ትንሽዬ የስልጣኔ ደሴት የተኮማተረበት አጋጣሚ ነበር። የዓለምን ሩብ ያስተዳድር የነበረው መንግሥት በፍጥነት የወደቀበት እና በሌላ ኃይል የተተካበት ክስተት።

የእንግሊዝ ኢምፓየር በብዙ ክፍለ ዘመናት ነበር የተገነባው። በብዙ ክፍለ ዘመናት የተገነባው ኢምፓየር ለመውደቅ ግን 11 ቀናት ነበር የፈጀበት። ያ የሆነው ደግሞ በአንድ የስልክ ጥሪ ብቻ ነበር። በዚያ የስልክ ጥሪ የዩናይትድ ስቴትስ መንግሥት ብሪታንያ በስዊዝ ቦይ የጀመረችውን ወታደራዊ ኦፕሬሽን በአስቸኳይ እንድታቆም ቀጭን ትዕዛዝ ያስተላለፈበት ታሪካዊ አጋጣሚ ነው። ያኔ የብሪታንያ ልዕለ-ኃያልነት ልምሾ ሆኖ የቀረበት አንድ ትልቅ ፖለቲካዊ ክስተት ነበር። የዩናይትድ ስቴትስ መንግሥት "ብሪታንያ በግብፅ እያደረገች ያለውን ኦፕሬሽን በአስቸኳይ ካላቆመች ፓውንድን መገበያያ ሳይሆን አንድ ተራ ውዳቂ ወረቀት አደርገዋለሁ" ነበር ያለው። በተጨማሪም ዩናይትድ ስቴትስ "ድምፅን በድምፅ የመሻር ሥልጣኔን ብሪታንያ ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) የድንገተኛ ጊዜ ብድር እንዳታገኝ እንደ አንድ ፖለቲካዊ መሣሪያ እጠቀመዋለሁ" በማለት አስጠነቀቀች።

በወቅቱ ብሪታንያ ምንም ምርጫ አልነበራትም። በእርግጥም ዩናይትድ ስቴትስ ይህን የምታደርግ ከሆነ ብሪታንያ ጊዜያዊ ወጪዎቿን እንኳ መሸፈን የማትችል አንድ ተራ ምፅዋተኛ ሀገር ሆና ነበር የምትቀረው። በዚህም ምክንያት ዓለምን ሲገዛ የነበረው ኢምፓየር እጅ ሰጠ። እጅ የሰጠውም ለጠላት አልነበረም፤ ይልቁንስ እጅ የሰጠው ለራሱ ድክመት እና ለብድር ነበር። ብሪታንያ በልዕለ-ኃያልነቷ ብዙ ጊዜ እንደማትቆይ ያን ጊዜ ነበር የገባት። ይህ ክስተት "የስዊዝ ቀውስ" ይባላል። ይህ የብሪታንያ ልዕለ-ኃያልነት ለዘላለም ተነቅሎ የወደቀበት እና በዓለም ዙሪያ ይንቀሳቀስ የነበረው ፖለቲካዊ እጇ የተቆረጠበት አጋጣሚ ነበር። ይህ የተደበቀው እና ማናችንም በትምህርት ቤት ያልተማርነው የምዕራባውያን ገመና ነው።

በእርግጥ ብሪታንያ በዚህ ቀውስ ብቻ አልነበረም የወደቀችው። ብሪታንያ መውደቅ የጀመረችው አስቀድማ ነው። ያ ሥልጣኔ የተገነባበትን ያህል ቀስ በቀስ ተቦርቡሮ በአጭር ጊዜ ውስጥ ተገርስሷል። ብሪታንያ ልክ ዩናይትድ ስቴትስ አሁን እየሠራች ያለውን ዓይነት የማይታረም ስህተት እየሠራች ነበር።

የብሪታንያ መነሳት እና የፓውንድ የበላይነት ታሪክ

በ1800 እ.ኤ.አ. ብሪታንያ የግሎባል ኢኮኖሚ መሪ (Master) ነበረች። የዓለም ሀብት ሁሉ ግምጃ ቤት እንደማለት ነው። በወቅቱ የብሪታንያ ፓውንድ አንድ ተራ መገበያያ ብቻ አልነበረም። አንድ ራሱን የቻለ የሀብት ሰነድ ነበር። በሁሉም የዓለም ጫፍ ሰዎች የሚገበያዩበት፣ የሀገራት ማዕከላዊ ባንኮች ሪዘርቭ የሚያከማቹበት፣ መንግሥታት የሀብታቸውን መጠን የሚለኩበት፣ በብሪታንያ ማዕከላዊ ባንክ ብቻ የሚንቀሳቀስ እና የዓለም ኢኮኖሚ የኮንትራክት ሰነድ ነበር። ይህ ደግሞ ብሪታንያን ልዕለ-ኃያል አድርጓታል።

በዚህም ምክንያት ብሪታንያ ከየትኛውም የዓለም ጫፍ ጥሬ ዕቃን በርካሽ ትገዛለች። ለወታደራዊ ተቋማትም በገፍ በጀት ትመድባለች። ሀገራትን ከዚህ ሥርዓት ማስወጣትም ማስገባትም ትችላለች። በፈለገችው ላይ ማዕቀብ ትጥላለች። የፈለገችውን ትደጉማለች። ምክንያቱም ፓውንድ የዓለም መገበያያ ነበር። ነገር ግን ይህ ኃይል ቀስ በቀስ ከሥሩ መናወጥ እና መሰባበር ጀመረ።

የዩናይትድ ስቴትስ መነሳት እና የኃይል ሽግግር

በ1800ዎቹ ዩናይትድ ስቴትስ የብሪታንያን ዱካ እግር በእግር እየተከተለች ነበር። ነገር ግን የዩናይትድ ስቴትስ ኢንዱስትሪዎች በብሪታንያ ኢንዱስትሪዎች ከፍተኛ ጫና ይደረግባቸው ነበር። በዚህ ጫና ውስጥ የዩናይትድ ስቴትስ የፈጠራ ኢንዱስትሪ ተመነደገ። ከብሪታንያ ቁጥጥር ውጭ እየሆነ መጣ። የዩናይትድ ስቴትስ ሀብት እያንጸባረቀ፣ የብሪታንያ ደግሞ እየደበዘዘ መምጣት ጀመረ። ሆኖም ግን የፓውንድ አቅም ብቸኛው መተማመኛ ነበር። የልዕለ-ኃያልነት ሥርዓቱ ከፓውንድ የተገነባ ስለነበር፣ ይህንን መገበያያ ገንዘብ መቀየር ለዩናይትድ ስቴትስ ኢኮኖሚ አማራጭ የሌለው አማራጭ ሆነ።

የመጀመሪያው የዓለም ጦርነት ሲፈነዳ ብሪታንያ ከፍተኛ የእዳ ጫና ውስጥ ገባች። በወቅቱ ብሪታንያ ትልቋ ተበዳሪ ስትሆን፣ ትልቋ አበዳሪ ደግሞ ዩናይትድ ስቴትስ ነበረች። ያኔ ብሪታንያ ምንም ለውጥ እንደማይኖር በመረዳት ይህንን እውነታ በጸጋ ለመቀበል ተገደደች። ውድቀቷን አሜን ብላ ተቀበለች።

የብሪታንያ ውድቀት ምክንያቶች

እ.ኤ.አ. በ1925 ብሪታንያ ትልቁን የፋይናንስ ስህተት የፈጸመችበትን ውሳኔ አሳለፈች። በክፍለ ዘመናት ውስጥ ይህ የብሪታንያ ትልቁ ስህተት ነበር። የፓውንድን አቅም ለመጠበቅ የወርቅ ክምችቷን ለማሳደግ ያሳለፈችው ውሳኔ ሳይሳካ ቀረ። የእዳዋ የወለድ መጠን ከፍተኛ ሆነ፤ ይህ ውሳኔ እድገቷን ለመጨረሻ ጊዜ ሰበረው። ያኔ የብሪታንያ ልዕለ-ኃያልነት ላይነሳ ለዘላለም ተቀበረ። በሀገሪቱ የሥራ ዕድል ጠፋ፤ የብሪታንያ ኤክስፖርት ውድ እና የማይቀመስ ሆነ። ብሪታንያ በዓለም ዙሪያ ያላትን ወታደራዊ ኃይል ለማስተዳደር ቀርቶ ወደ አንድ ማዕከል እንኳ መሰብሰብ ተሳናት።

ብሪታንያ በአንደኛው እና በሁለተኛው የዓለም ጦርነቶች ድል ብታደርግም፣ ዋጋው ግን እጅግ ከፍተኛ ነበር። ጦርነቶቹን ለመወጣት ስትል ከአሜሪካ ከፍተኛ መጠን ያለው ብድር ተበደረች። ይህም ብሪታንያን ከዓለም ትልቋ "አበዳሪ" ወደ ዓለም ትልቋ "ተበዳሪ" ሀገርነት ለወጣት። ሀብቷ በሙሉ ለጦርነት መሣሪያ እና ለወታደሮች ደመወዝ በመዋሉ፣ የሀገር ውስጥ ኢንዱስትሪዋ እየዛለ መጣ።

በ19ኛው ክፍለ ዘመን ፓውንድ (Pound Sterling) የዓለም ብቸኛ መገበያያ ነበር። ሆኖም በ1925 የብሪታንያ መንግሥት የፓውንድን ዋጋ ከወርቅ ጋር ለማስተሳሰር (Gold Standard) የወሰደው ውሳኔ ትልቅ ስህተት ነበር። ይህም የብሪታንያ ምርቶች በዓለም ገበያ ላይ እጅግ ውድ እንዲሆኑ አደረገ። ኤክስፖርት (ወደ ውጭ መላክ) በመቀነሱ በሀገር ውስጥ ሥራ አጥነትና ድህነት ተስፋፋ። በተቃራኒው አሜሪካ እና ዶላር የዓለምን የፋይናንስ መሪነት እንዲረከቡ በር ከፈተ።

ብሪታንያ የኢንዱስትሪ አብዮት መገኛ ብትሆንም፣ በ20ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ ግን አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን (እንደ ኤሌክትሪክ እና የጅምላ ምርት/Mass Production) በመቀበል ረገድ ከአሜሪካ እና ከጀርመን ወደኋላ ቀረች። የብሪታንያ ፋብሪካዎች አረጁ፤ ምርታማነታቸውም ቀነሰ። ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ በሕንድ፣ በአፍሪካ እና በመካከለኛው ምስራቅ የነበሩ የብሪታንያ ቅኝ ግዛቶች የነፃነት ጥያቄ አነሱ። ብሪታንያ እነዚህን ግዛቶች በወታደራዊ ኃይል ለመቆጣጠር የሚያስችል የኢኮኖሚ አቅም አልነበራትም። ግዛቶቿን አንድ በአንድ ስታጣ፣ የጥሬ ዕቃ ምንጯ እና የገበያ የበላይነቷ አብሮ ከሰመ።

የስዊዝ ቀውስ (1956)

ይህ ክስተት የብሪታንያን ልዕለ-ኃያልነት በይፋ የቀበረ አጋጣሚ ነው። ብሪታንያ ከፈረንሳይ እና ከእስራኤል ጋር በመሆን ግብፅን በወረረች ጊዜ፣ አሜሪካ ድርጊቱን አልደገፈችውም። አሜሪካ "ወታደሮቻችሁን ከግብፅ ካላወጣችሁ የብሪታንያን ፓውንድ ዋጋ አሳጣዋለሁ (Crash the currency)" በማለት ትልቅ ማስጠንቀቂያ ሰጠች። እንዲሁም ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) ልታገኝ የነበረውን አስቸኳይ ብድር አገደች። ብሪታንያ ለራሷ ወጪ መሸፈኛ እንኳ ገንዘብ ስላልነበራት፣ በአሜሪካ የአንድ ስልክ ጥሪ ትዕዛዝ ወታደሮቿን ለማስወጣት ተገደደች። ያኔ ዓለም ብሪታንያ ከአሁን በኋላ ልዕለ-ኃያል ሳይሆን፣ የአሜሪካ ተከታይ መሆኗን አወቀ።

የአሜሪካ ልዕለ-ኃያልነት ምስረታ

አሜሪካ ልዕለ-ኃያል እንድትሆን ትልቁን በር የከፈቱላት የዓለም ጦርነቶች ናቸው። ጦርነቶቹ በአውሮፓ እና በእስያ መሬት ላይ ሲካሄዱ፣ አሜሪካ ግን ከጦርነቱ ቀጠና ርቃ በሰላም ንፍቀ ክበብ ውስጥ ነበረች። አሜሪካ ለብሪታንያና ለሌሎች ወዳጆቿ የጦር መሣሪያና ምግብ በማቅረብ እጅግ ግዙፍ ሀብት አከማቸች። ወደ አውሮፓ ሀገራት የሚፈሰው ወርቅ በሙሉ ወደ አሜሪካ ገባ። በጦርነቱ መጨረሻ አሜሪካ የዓለምን 70% የወርቅ ክምችት በቁጥጥሯ ሥር አደረገች።

የብሬተን ውድስ (Bretton Woods) ስምምነት

እ.ኤ.አ. በ1944፣ የሁለተኛው የዓለም ጦርነት ከመጠናቀቁ በፊት፣ 44 ሀገራት አሜሪካ ውስጥ ተሰብስበው አዲስ የፋይናንስ ሥርዓት መሰረቱ። ሁሉም የዓለም ገንዘቦች በዶላር እንዲተመኑ፣ ዶላር ደግሞ በወርቅ እንዲደገፍ ተወሰነ። በዚህም ዶላር የዓለም "ሪዘርቭ" ገንዘብ ሆነ። ይህም አሜሪካ የፈለገችውን ያህል ገንዘብ በማተም ዓለምን እንድትቆጣጠር ታላቅ ፖለቲካዊ ጡንቻ ሰጣት።

አሜሪካ በ20ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ የ"ጅምላ ምርት" (Mass Production) ስልትን ፈጠረች። ሄንሪ ፎርድ የመኪና ምርትን ተደራሽ እንዳደረገው ሁሉ፣ አሜሪካ በቴክኖሎጂ ዘርፍ (አውሮፕላን፣ ኤሌክትሮኒክስ እና በኋላም ኮምፒውተር) ዓለምን ቀደመች። ብሪታንያ በአሮጌ ፋብሪካዎቿ ስትታገስ፣ አሜሪካ በአዳዲስ የፈጠራ ሥራዎች ገበያውን ተቆጣጠረች።

የማርሻል ፕላን (The Marshall Plan)

ከጦርነቱ በኋላ አውሮፓ በድህነትና በውድመት ውስጥ ነበረች። አሜሪካ "የማርሻል ፕላን" በሚባል ፕሮጀክት ቢሊዮን ዶላሮችን ለአውሮፓ ሀገራት በብድርና በእርዳታ ሰጠች። ይህ እርዳታ አውሮፓን መልሶ እንዲገነባ ቢረዳም፣ በሌላ በኩል ግን አውሮፓ በአሜሪካ ኢኮኖሚ ሥር እንድትወድቅና የአሜሪካ ምርቶች ገበያ እንድትሆን አደረጋት። አሜሪካ በዓለም ዙሪያ በመቶዎች የሚቆጠሩ ወታደራዊ ቤዞችን (Military Bases) በመገንባት የባህርና የሰማይ መንገዶችን ተቆጣጠረች። ከዚህ በተጨማሪም ሆሊውድ፣ ሙዚቃ እና የምግብ ምርቶቿ (እንደ ኮካ ኮላ) የዓለምን ሕዝብ አስተሳሰብ ከአሜሪካ ጋር እንዲተሳሰር አደረጉ።

የፕሬዝዳንት ትራምፕ ሚና እና የአሜሪካ ተሰሚነት መዳከም

ዩናይትድ ስቴትስ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ተሰሚነቷ እና ፖለቲካዊ አቅሟ ቀንሷል። የዩናይትድ ስቴትስ ዓለም አቀፋዊ ተሰሚነት እና ዲፕሎማሲያዊ ተፅዕኖ ውኃ የበላው በ2016 ፕሬዝዳንት ትራምፕ ሲመረጡ ነው። ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከወትሮዎቹ የዩናይትድ ስቴትስ መሪዎች በተለየ ሁኔታ፣ ራሷ ዩናይትድ ስቴትስ ጸንታ የቆመችበትን የግሎባላይዜሽን ሥርዓት የሚዘረጥጡ፣ ዓለም አቀፍ ተቋማትን እና ኮርፖሬቶችን የሚያከስሙ እና የዩናይትድ ስቴትን ሀገረ-መንግሥት ሥርዓት በአዲስ የብሔርተኛ ሥርዓት ለመተካት የሚጥሩ ፕሬዝዳንት ናቸው። ፕሬዝዳንቱ ምስጢር የማይቋጥሩ እና የሚዘባርቁ እንዲሁም ንግግራቸው እርስ በእርሱ የሚጠላለፍ በመሆኑ የአሜሪካ ተደማጭነት በወትሮው መንገድ መቀጠል አልቻለም።

ፕሬዝዳንት ትራምፕ እንዲመረጡ ሩሲያ እጇን አስገብታለች ይባላል። ምናልባትም ይህ እውነት ሊሆን የሚችልበት በርካታ ምክንያቶች ይኖራሉ። ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከተመረጡ በኋላ የአሜሪካ ተደማጭነት ሲከስም፣ በተቃራኒው የሩሲያ ተፅዕኖ በተለይም በምስራቁ የዓለማችን ክፍል እያደገ መጣ። ሩሲያ አውሮፓውያንን ከአሜሪካ ጥላ ሥር ለመነጠል የተጠቀመችበት ፖለቲካዊ ታክቲክም ሊሆን ይችላል። ብቻ ትራምፕ ከተመረጡ በኋላ የዩናይትድ ስቴትን የዘላለም ፖሊሲ እየተቃረኑ የዲሞክራቶቹን መሪዎች ፕሮጀክቶች በማፍረስ በጥቃቅን ጉዳዮች ላይ ተጠምደው የሚፈይድ ነገር ሳይሠሩ ከሥልጣን ተሰናበቱ። ፕሬዝዳንት ባይደንም ያንን ውድቀት መታደግ አልቻሉም። በእነዚህ ጊዜያት የቻይና ምርቶች የአሜሪካን ገበያዎች ተቆጣጠሩ። የቻይና አቅም የዩናይትድ ስቴትን ልዕለ-ኃያልነት ለመተካት ምንም አልቀረውም ነበር። የትራምፕ ለሁለተኛ ጊዜ መመረጥ የዩናይትድ ስቴትን ኢኮኖሚ በቻይና ከመዋጥ ቢታደገውም፣ የአሜሪካን ግሎባል ፓወር ሰባብሮታል።

የትራምፕ ዳግም መመለስ እና የ"ብቸኝነት" ፖሊሲ (Isolationism)

ትራምፕ ለሁለተኛ ጊዜ ሥልጣን ላይ ሲወጡ የወሰዱት "አሜሪካ ትቅደም" (America First) ፖሊሲ፣ ለበርካታ አስርት ዓመታት የቆየውን የምዕራባውያን ጥምረት (NATO) አዳከመው። አሜሪካ ከዓለም አቀፍ የንግድ ስምምነቶች ስትወጣና ከፍተኛ ታሪፍ (Tariff) በቻይና ምርቶች ላይ ስትጥል፣ ቻይና ደግሞ በተቃራኒው የ (Belt and Road) ፕሮጀክቷን በማስፋት የአፍሪካን፣ የእስያንና የላቲን አሜሪካን ገበያ በቁጥጥሯ ሥር አደረገች።

አሜሪካ ለብዙ ዓመታት በዓለም ላይ የነበራት ተሰሚነት የመነጨው ከኔቶ (NATO) እና መሰል የጥምረት ስምምነቶች ነበር። ትራምፕ አጋሮቻቸውን (እንደ ጀርመን እና ፈረንሳይ ያሉ) በገንዘብ እና በመከላከያ ወጪዎች ምክንያት በመጫናቸው፣ አውሮፓ አሜሪካን እንደ አስተማማኝ ባልደረባ ማየቷን እንድታቆም አድርጓል። ይህ ደግሞ ብሪታንያ በ1956 አጋሮቿን እንዳጣችው ሁሉ፣ አሜሪካም ብቻዋን እንድትቀር (Isolationism) መንገድ ከፍቷል።

የግሎባላይዜሽን ሥርዓትን መናድ

አሜሪካ የዓለም መሪ የሆነችው በዶላር እና በዓለም አቀፍ ንግድ መረብ ነው። ትራምፕ ከተለያዩ የንግድ ስምምነቶች (እንደ TPP ያሉ) በመውጣታቸው እና በቻይና ላይ የንግድ ጦርነት በመክፈታቸው፣ ዓለም ከአሜሪካ ቁጥጥር ውጭ የሆኑ አማራጭ የንግድ መስመሮችን እንድትፈልግ አነሳስተዋል። ውጤቱ ቻይና ይህንን ክፍተት በመጠቀም በኤዥያ እና በአፍሪካ ያላትን የኢኮኖሚ ተፅዕኖ በከፍተኛ ፍጥነት እንድታሳድግ ዕድል ሰጥቷታል።

የዲፕሎማሲያዊ ተሰሚነት (Soft Power) መጥፋት

ልዕለ-ኃያልነት በጠመንጃ ብቻ ሳይሆን በንግግር እና በሥነ-ልቦና የበላይነትም የሚገለጽ ነው። የትራምፕ የንግግር ዘይቤ፣ የዲፕሎማሲያዊ ፕሮቶኮሎችን አለማክበር እና ዓለም አቀፍ ስምምነቶችን (እንደ የፓሪስ የአየር ንብረት ስምምነት) ማፍረሳቸው፣ አሜሪካ ለዓለም የምትሰጠውን "የሥርዓት እና የሕግ አክባሪነት" ገጽታ አበላሽቶታል። ይህ ደግሞ በ2026 ለምናየው የአሜሪካ ዲፕሎማሲያዊ ተፅዕኖ መዳከም ትልቁን ድርሻ ይይዛል።

ትራምፕ በሥልጣን ላይ በነበሩበት ጊዜ እና ከዚያም በኋላ፣ በአሜሪካ ማህበረሰብ ውስጥ ከፍተኛ የሆነ የርዕዮተ-ዓለም ክፍፍል ተፈጥሯል። ልክ እንደ ብሪታንያ ውድቀት፣ አንድ ሀገር በውስጧ በዘር፣ በፖለቲካ እና በኢኮኖሚ ጥቅሞች ስትከፋፈል፣ ትኩረቷ ከዓለም አቀፍ መሪነት ወደ ውስጥ "ቤት ማፅዳት" ላይ ይውላል። አሜሪካ አሁን በራሷ የፖለቲካ ቀውስ ተጠምዳ ባለችበት ወቅት፣ ቻይና እና ሩሲያ በምስራቁ ዓለም የራሳቸውን አዲስ የፖለቲካ ጎጆ ቀልሰዋል።

የዶላር የጦር መሣሪያነት (Weaponization of the Dollar)

የትራምፕ አስተዳደር በኢራን እና በሌሎች ሀገራት ላይ የጣለው ጠንካራ የፋይናንስ ማዕቀብ፣ ዓለም ዶላርን መፍራት እንድትጀምር አድርጓል። ይህም በ2026 እውን እየሆነ ላለው "ዲ-ዶላራይዜሽን" (De-dollarization) ወይም ከዶላር ውጭ የመገበያየት ፍላጎት መነሻ ሆኗል።

ተመሳሳይ የውድቀት መንገድ /ከተራራ ገተንተራ/

አብዛኞቹ ሥልጣኔዎች ተመሳሳይ የውድቀት መንገድ ተከትለው እንደከሰሙ ይነገራል። እንደ ፈረንጆቹ አቆጣጠር በ2026 እነዚህ ስህተቶች በዩናይትድ ስቴትስ ተደግመዋል። የብሪታንያ ፓውንድ በወርቅ ክምችት ስህተት እንደወደቀ ሁሉ፣ የዩናይትድ ስቴትስ ዶላርም በ2020ዎቹ አጋማሽ ላይ ታላቅ ፈተና ገጥሞታል። ዩናይትድ ስቴትስ ዶላርን እንደ ፖለቲካዊ መሣሪያ በመጠቀም በሩሲያ እና በሌሎች ሀገራት ላይ የጣለችው ማዕቀብ፣ ዓለምን "ተለዋጭ መንገድ" እንድትፈልግ አስገደዳት። በ2024 እና 2025፣ የብሪክስ (BRICS) አባል ሀገራት ቁጥር መጨመር እና በራሳቸው መገበያያ ገንዘብ ግብይት መጀመራቸው፣ የዶላርን የዓለም መጠባበቂያ ገንዘብነት (Reserve Currency) ክፉኛ መታው። ዶላር ሲዳከም፣ አሜሪካ የውጭ እዳዋን ለመሸፈን የምታትመው ወረቀት ዋጋ አጣ። ልክ እንደ 1956ቱ የብሪታንያ ፓውንድ፣ ዶላርም ከፖለቲካዊ ጡንቻነት ወደ ተራ ወረቀትነት መለወጥ ጀመረ።

አሜሪካ በአሁኑ ወቅት ከ38 ትሪሊዮን ዶላር በላይ እዳ አለባት። ይህ እዳ በየቀኑ እየጨመረ ሲሆን፣ መንግሥት ለብድሩ ወለድ ብቻ የሚከፍለው ገንዘብ ከመከላከያ በጀቱ ጋር እየተስተካከለ ነው። ውጤቱ ልክ ብሪታንያ በ1950ዎቹ ለወታደራዊ ኃይሏ የምታወጣው ገንዘብ እንደጠፋባት ሁሉ፣ አሜሪካም እዳዋን ለመክፈል ስትል በዓለም ዙሪያ ያላትን ተፅዕኖ ለመቀነስ ትገደዳለች።

የአሜሪካ ኢኮኖሚ ከእውነተኛ ምርት (Manufacturing) ይልቅ ወደ ፋይናንስ እና ግምታዊ ግብይት (Wall Street) አዘንብሏል። አሜሪካ ዕቃዎችን ከማምረት ይልቅ የሌሎችን ሀገራት ምርቶች በዶላር መግዛትን መርጣለች። ይህ ደግሞ የሀገሪቱን የኢንዱስትሪ መሠረት አዳክሞታል። በተቃራኒው ቻይና "የዓለም ፋብሪካ" በመሆን እውነተኛውን የሀብት ምንጭ ተቆጣጥራለች። ብሪታንያም በ19ኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ ምርቷ ሲዳከም ውድቀቷ እንደጀመረው ሁሉ፣ አሜሪካም ያው መንገድ ላይ ነች።

የውስጥ መፈራረስ እና ወታደራዊ ጀብዱዎች

ዩናይትድ ስቴትስ በ20ኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ ላይ የነበራትን የኢኮኖሚ ጥንካሬ፣ በ21ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ በወታደራዊ ጀብዱዎችና በውጭ ጦርነቶች አባክናዋለች። ልክ ብሪታንያ በመጀመሪያው የዓለም ጦርነት ወቅት ትልቋ ተበዳሪ እንደሆነች ሁሉ፣ ዩናይትድ ስቴትስም በ2020ዎቹ መገባደጃ ላይ የዓለም ትልቋ ተበዳሪ ሆናለች። የእዳዋ መጠን ከጠቅላላ ምርቷ (GDP) ጋር ሲነጻጸር አስፈሪ ደረጃ ላይ ደርሷል።

አሜሪካ ውስጥ የእፅ ሱስ (Opioid Crisis) በየዓመቱ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶችን እየገደለ የሰው ኃይል ምርታማነትን እየቀነሰ ነው። የሀብት ክፍተት፦ ጥቂት ቢሊየነሮች የሀገሪቱን ሀብት ሲቆጣጠሩ፣ መካከለኛው መደብ (Middle Class) እየጠፋ መጥቷል። ይህ ደግሞ ለፖለቲካዊ አለመረጋጋት እና ለሕዝባዊ አመፅ ትልቅ ምክንያት ሆኗል።

ለአስርተ ዓመታት አሜሪካ በሳይንስ እና ቴክኖሎጂ (NASA, Silicon Valley) ዓለምን ትመራ ነበር። አሁን ግን ይህ የበላይነት እየተፈተነ ነው። ቻይና በ5G፣ በኳንተም ኮምፒውቲንግ እና በአረንጓዴ ኢነርጂ (የኤሌክትሪክ መኪናዎች እና ባትሪዎች) አሜሪካን እየቀደመች ነው። የዓለም ምርጥ ሳይንቲስቶች ከቪዛ ጥብቅነትና በዘረኝነት ስጋት ምክንያት ወደ ሀገራቸው እየተመለሱ ወይም ሌላ አማራጭ እየፈለጉ ነው። የብሪታንያ ውድቀት የተፋጠነው ኢንዱስትሪዎቿ ከዘመኑ ጋር መራመድ ሲሳናቸው ነበር። አሜሪካም አሁን የቴክኖሎጂ ፈጠራዎች በከፍተኛ የዋጋ ግሽበት እና በሙያተኛ እጥረት ሲዳከሙ፣ ቻይና እና የእስያ ታዳጊ አገራት በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI), በኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች እና በቺፕ ማምረቻ ቴክኖሎጂዎች ላይ የላቀ እርምጃ ወስደዋል።

ይዮጥላል...

Address

Addis Ababa

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when የኢትዮጵያ ሙስሊሞች መብት ተሟጋች ድርጅት/ /Ethiopian muslim rights gaurd posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Share