Keranio Media ቀራኒዮ ሚዲያ

Keranio Media ቀራኒዮ ሚዲያ Contact information, map and directions, contact form, opening hours, services, ratings, photos, videos and announcements from Keranio Media ቀራኒዮ ሚዲያ, Haile Gebresilassei Road, Addis Ababa.

ኒቆዲሞስ፡ የሌሊቱ ምስጢርና የነፍስ ዳግም ልደት​የዓብይ ጾም ሰባተኛው ሳምንት "ኒቆዲሞስ" ይባላል። ይህ ሳምንት በጾሙ መጨረሻና በሕመማት ሳምንት መጀመሪያ መካከል ያለ፣ የብርሃንና የጥልቅ ...
29/03/2026

ኒቆዲሞስ፡ የሌሊቱ ምስጢርና የነፍስ ዳግም ልደት

​የዓብይ ጾም ሰባተኛው ሳምንት "ኒቆዲሞስ" ይባላል። ይህ ሳምንት በጾሙ መጨረሻና በሕመማት ሳምንት መጀመሪያ መካከል ያለ፣ የብርሃንና የጥልቅ እውነትን ፍለጋ ሂደት ሲሆን ታሪኩ የሚጀምረው በዝምታ በተዋጠችው የኢየሩሳሌም ሌሊት ነው።............
​ኢየሩሳሌም ተኝታለች። ነገር ግን የአይሁድ መምህርና የሸንጎ አባል የሆነው ኒቆዲሞስ እንቅልፍ አልወሰደውም። በልቡ ውስጥ የሚነድ ጥያቄ አለ፤ ያ ጥያቄ ደግሞ "ይህ ድንቅ ተአምራትን የሚያደርግና በሥልጣን የሚያስተምር ሰው ማነው?" የሚል ነበር። ኒቆዲሞስ ክብሩንና ማዕረጉን የሚወድ ሰው ቢሆንም፣ እውነቱን ለማግኘት ግን ጥማቱ በረታበት። በቀን ቢመጣ አይሁድ እንደሚቃወሙት ያውቃል፤ በመሆኑም ክብሩንና ፍርሃቱን ተሸክሞ በሌሊት ጨለማ ተሰውሮ ወደ ጌታ መጣ።

​ኒቆዲሞስ ጌታችን ባለበት ስፍራ ደርሶ፣ በትሕትና እንዲህ አለው፦ "መምህር ሆይ! እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ካልሆነ በቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል ማንም የለምና መምህር ሆነህ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን።"

ጌታችን ግን የኒቆዲሞስን ውጫዊ ምስጋና አልተቀበለም፤ ይልቁንም ወደ ነፍሱ ጥልቀት ገባ። ኒቆዲሞስ የመጣው ስለ ተአምራቱ ሊጠይቅ ነበር፤ ጌታ ግን የነገረው ስለ መንግሥተ ሰማያት መግቢያ መንገድ ነበር። እንዲህም አለው፦

​"እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም።"

​የሕግ መምህሩ ኒቆዲሞስ ግራ ተጋባ። በሥጋዊ አእምሮው አስቦ እንዲህ ሲል ጠየቀ፦ "ሰው ካረጀ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል? ዳግመኛ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ መወለድ ይችላልን?" ጌታችንም የሰማያዊውንና የመንፈሳዊውን ዓለም በር ከፈተለት፦

​"ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም። ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፥ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነው።"

​በዚያች ሌሊት ኒቆዲሞስ የታደሰ ማንነትን ምስጢር ተማረ። ሰውነት በሥጋ ብቻ ሳይሆን በመንፈስ ዳግመኛ መፈጠር እንዳለበት ተገነዘበ። ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ይህንን " ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ ሖረ ኀቤሁ ዘስሙ ኒቆዲሞስ ወይቤሎ ለኢየሱስ ረቢ ሊቅ ንሕነ ነአምን ብከ ከመ እምኀበ አብ መጻእከ ከመ ትኩን መምህረ ዕጓለ አንበሳ ሰከብከ ወኖምከ አንሥአኒ በትንሣኤከ" እያለ በጣዕመ ዜማው ሲያዜመው፣ እኛም እንደ ኒቆዲሞስ ከዓለም ጫጫታ ርቀን በሌሊት ጸሎት ወደ ጌታ እንድንቀርብ ያሳስበናል።

​፩ . ከምስጢር ተማሪነት ወደ ታማኝ ምስክርነት

​የኒቆዲሞስ ታሪክ በዚያች ሌሊት አላበቃም። ያ በሌሊት ተሸሽጎ የመጣው መምህር፣ ቆይቶ ጌታችን በአይሁድ ሸንጎ ፊት ሲከሰስ "ሕጋችን አስቀድሞ ሳይሰማው ይፈርዳልን?" ብሎ በድፍረት ተከራከረ። ከሁሉም በላይ ደግሞ በዕለተ ዓርብ ሁሉም ደቀ መዛሙርት በፈሩና በሸሹ ጊዜ፣ ኒቆዲሞስ ግን ከዮሴፍ ጋር ሆኖ መቶ ንጥር የሚያህል የከርቤና የዓልባላ ቅልቅል ይዞ በመምጣት የጌታን ሥጋ በክብር ገነዘ። በሌሊት ተሸሽጎ የጀመረው ጉዞ፣ በመስቀሉ ስር በይፋ ፍቅርን በመግለጽ ተፈጸመ።

​💡 ከኒቆዲሞስ የምንማረው ታላቅ ቁምነገር፦

​የትሕትና መንገድ፦ ኒቆዲሞስ ትልቅ መምህር ቢሆንም፣ እውነትን ፍለጋ ግን እንደ ተማሪ በጌታ እግር ስር ተቀመጠ። እኛስ ለማወቅ ምን ያህል ትሁት ነን?

​ከኃጢአት ጨለማ መውጣት፦ ሌሊቱ የኃጢአታችንና የድንቁርናችን ምሳሌ ነው። ኒቆዲሞስ ከሌሊቱ ጨለማ ወጥቶ ወደ ዓለም ብርሃን እንደመጣ፣ እኛም በዚህ ጾም ከጨለማ ሥራችን ተለይተን ወደ ብርሃኑ መቅረብ ይገባናል።

​የአዲስ ልደት ፍሬ፦ ንስሐና ጥምቀት ዳግመኛ የምንወለድባቸው መንገዶች ናቸው። ካረጀው የጥል፣ የቂምና የክፋት ማንነት ወጥተን አዲስ ፍጥረት ለመሆን ይህ ሳምንት የመጨረሻው ጥሪ ነው።

​ማጠቃለያ፦

ኒቆዲሞስ የእያንዳንዳችን ነፍስ ምሳሌ ነው። ሁላችንም በውስጣችን እውነትን እንጠማለን። ጌታችን ደግሞ ዛሬም በቃሉ "ና! ዳግመኛ ተወለድ፤ አዲስ ሰው ሁን" ይለናል። ይህ ሳምንት የአሮጌው ማንነታችን ማብቂያ፣ የአዲሱ መንፈሳዊ ሕይወታችን ጅማሬ ይሁንልን።

​መልካም የኒቆዲሞስ ሳምንት!

ከገነተ ጽጌ ሚድያ የተወሰደ።
#ኪዳንሚዲያ #ተዋሕዶ #ኦርቶዶክሳዊ #መዝሙር

18/03/2026

#ኪዳንሚዲያ #ተዋሕዶ #ኦርቶዶክሳዊ #መዝሙር

Keranio Media ቀራኒዮ ሚዲያ

17/03/2026

#ኪዳንሚዲያ #ተዋሕዶ #ኦርቶዶክሳዊ #መዝሙር

የመምህር ዘለዓለም ወንድሙ የአሸኛኘትና የስንብት  መርሐ ግብርን አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጠመጋቢት 1 ቀን 2018 ዓ.ም ።"እመኒ ሐየውነ ወእመኒ ሞትነ ለእግዚአብሔር ንሕነ።""እንግዲህ...
10/03/2026

የመምህር ዘለዓለም ወንድሙ የአሸኛኘትና የስንብት መርሐ ግብርን አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጠ
መጋቢት 1 ቀን 2018 ዓ.ም ።

"እመኒ ሐየውነ ወእመኒ ሞትነ ለእግዚአብሔር ንሕነ።"
"እንግዲህ በሕይወት ሆነን ብንኖር ወይም ብንሞት የጌታ ነን።" ሮሜ 14÷8
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ እንዳለ
በሕይወቱ ዘመን ሁሉ በክርስቶስ ኖሮ ከክርስቶስ ጋር ለመኖር ናፍቆ የሄደውን የወንድማችንን እና የመምህራችንን ዘለዓለም ወንድሙን እንዲህ እንሸኘው ይኼንን ጋዜጣዊ መግለጫ እንሰጣለን።
መምህራችን መምህር ዘለዓለም ወንድሙ የእረፍት ዜናው ከተሰማበት ጊዜ አንስቶ መላው ኦርቶዶክሳውያን በሙሉ በጥልቅ ሐዘን ውስጥ ገብተዋል። መምህር ዘለዓለም ወንድሙ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያንን በታማኝነት ያገለገለ የሕይወት ዘመኑን ሙሉ መልካም የሆነ፤ ክርስቲያናዊ ጠባዩን ያልቀየረ ለብዙዎቹ ምሳሌና አርአያ ሆኖ የኖረ የወንጌልን ችቦ በመላው ዓለም ያቀጣጠለ ታላቅ መምህር ነው ። ስለዚህ ይኼንን ወንድማችንን በልዩ ስነ ሥርዓት የሕይወት ዘመን መልካም አገልግሎቱን ታሳቢ በማድረግ እና የቤርስቲያኒቱን ክብር በሚመጥን መልኩ በታላቅ የአሸኛኘት ስነ ሥርዓት ለመሸኘት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት እና በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ይሁንታ ኮሚቴ ተዋቅሮ ሥራዎችን ሲሠራ ቆይቷል።
ከዚህ በመነሳት የአሸኛኘት ስነ ሥርዓቱ ከቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ጀምሮ እስከ መንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ድረስ ስርዓቱን የጠበቀ ይሆን ዘንድ አሸኛኘቱ የሚከተሉትን ሂደቶች የሚከተል መሆኑን እናሳውቃለን።
1. የመምህር ዘለዓለም ወንድሙ አስከሬን ረቡዕ መጋቢት 2 ቀን 2018 ዓ ም ከአሀገረ አሜሪካ ተነስቶ ጉዞ ወደ ኢትዮጵያ የሚያደርግ ይሆናል።
2. ሐሙስ መጋቢት 3 ቀን 2018 ዓ ም አስከሬኑ ከጠዋቱ 12 :00 ላይ አዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ይደርሳል። በዛም በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እየተመራ የወንድማችን ወዳጅ ዘመዶች የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የገዳማትና አድባራት ሊቃውንት ጥቅ ድርባቸውን ለብሰው አቀባበል የሚያደርጉለት ይሆናል። በቦሌ ዓለም አቀፍ ማረፊያ የሚገኙት የተመረጡ እና ፈቃድ የተሰጣቸው አካላት ብቻ ናቸው።
3. ከጠዋቱ 1:00 ሰዓት ጀምሮ ከብሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት ጀምሮ እስከ ቦሌ ደ/ሳሌም መድሐኔዓለም ድረስ በሊቃውንተ ቤተክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤት ዘማርያን እና በምእመናን ታጅቦ ወደ ቦሌ ደ/ሳሌም መድሐኔዓለም ካቴድራል ጉዞ ያደርጋል።
4. በቦሌ ደብረ ሳሌም መድሐኔዓለም ካቴድራል አጭር ቆይታ ካደረገ በኋላ ቀጥታ በመለከት ድምጽ ነጋሪት እየተጎሰመ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቃውንት በመምህራነ ወንጌል በሰንበት ትምህርት ቤት ወጣት ዘማርያን እና በበርካታ ምእመናን ታጅቦ ከጠዋቱ 3:00 ጀምሮ እስከ 5:00 ሰዓት ድረስ መስቀል አደባባይ ይደረሳል
5. ከጠዋቱ 5:00 ሰዓት ጀምሮ በመስቀል አደባባይ የተለያዩ የአሸኛኘት መርሐግብሮች የሚከናወኑ ይሆናል ።

20/02/2026

#ተዋሕዶ #ኦርቶዶክሳዊ #መዝሙር

20/02/2026

I got over 20,000 reactions on my posts last week! Thanks everyone for your support! 🎉

“መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ”  በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ኣሐዱ አምላክ አሜን !!በሀገር ውስጥና በልዩ ልዩ ክፍለ ዓለማት የምትገኙ ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ፡-በመዋዕለ ጾሙ ሰይጣንንና...
15/02/2026

“መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ”
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ኣሐዱ አምላክ አሜን !!
በሀገር ውስጥና በልዩ ልዩ ክፍለ ዓለማት የምትገኙ ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ፡-
በመዋዕለ ጾሙ ሰይጣንንና መስሓቲ ተግባሩን ድል በማድረግ ድል እንድንነሣ ያደረገን ጌታችን ኣምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለሁለት ሺሕ ዓሥራ ስምንት ዓመተ ምሕረት ጾመ ኣርብዓ በሰላም ኣደረሰን አደረሳችሁ!!
‹‹ወልበሱ ወልታ እግዚአብሔር በዘትክሉ ተቃውሞቶ ለመናግንተ ሰይጣን፤ የሰይጣንን ሽንገላ መቃወም ትችሉ ዘንድ የእግዚአብሔርን ጋሻ ልበሱ›› (ኤፌ.፮፥፲፩)፤
እኛ ሰዎች ቀዋሚና ምሕረት የለሽ ጠላት እንዳለን እናውቃለን፤ ይህ ጠላት ሰይጣን፣ ዲያብሎስ፣ክፉ መንፈስ፣ ርኩስ መንፈስ ተብሎ እንደሚጠራም ቅዱስ መጽሓፍ ነግሮናል፤ዲያብሎስ ከጥንት ጀምሮ በክፉ ሽንገላው ሰዎችን ሲጥል ኖሮኣል፤ ኣሁንም ከዚህ ክፉ ተግባሩ ኣልታቀበም፤ ለወደፊቱም ይታቀባል ተብሎ ኣይጠበቅም፤ ጌታችን በዚህ ዓለም በሥጋ በተገለጠ ጊዜም ይህ ክፉና ርኩስ መንፈስ በሽንገላ ቃሉ ጌታችንን ሊጥል ያልተሳካ ሙከራ አድርጎኣል፡፡
ርኩሱ መንፈስ ጾም መንፈሳዊ ኃይልን እንደሚያቀዳጅ ያውቃልና፣ ጌታችን ምንም ሳይበላና ሳይጠጣ ኣርባ ቀንና ኣርባ ሌሊት መጾሙን ተመልክቶ፣ በሽንገላ ቃሉ ሊጥለው ሙከራ አድርጎኣል፤ ይህንን ያደረገበት ዋና ምክንያትም ጾም መንፈሳዊ ኃይል መሆኑን በውል ያውቃልና በጾም ኃይል ከእጄ ያመልጣል ብሎ በማሰቡ ነው፤ ይሁን እንጂ ሰይጣን የሰውን ደካማ ጠባይ በመጠቀም ያስለመደው ሽንገላ፣በተዋሕዶ ሰውም ኣምላክም በሆነው ጌታችን ላይ ሊሳካለት ባለመቻሉ ተሸንፎና ተስፋ ቆርጦ ሊሄድ ችሎኣል፡፡
የተወደዳችሁ ሕዝበ ክርስቲያን ልጆቻችን!
የጌታችን ድል አድራጊነት ያስተማረን ብዙ ነገር አለ፤በዚህ ተግባራዊ ትምህርቱ እኛ ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስን ድል የምናደርግባቸው ሁለት መሣሪያዎችን በዋናነት አሳይቶናል፤ እነሱም የእግዚአብሔርን ጋሻ መልበስና በጾም መንፈሳዊ ኃይልን መቀዳጀት ናቸው፡፡
ሁሌም እንደምንማረው በውስጣችን ሁለት ተቃራኒ ነገሮች ኣሉ፤ እነሱም ፍትወተ ሥጋና ፍትወተ መንፈስ ናቸው፤ እነኝህ ሁለት ነገሮች ኣንዱ ላንዱ ፍጹም ተቃራኒ መሆናቸውን ቅዱስ መጽሓፍ እንዲህ በማለት ያስረዳል፡-‹‹ እስመ ሥጋኒ ይፈቱ ዘኢይፈቱ መንፈስ፤ ወመንፈስኒ ይፈቱ ዘኢይፈቱ ሥጋ፤ ወይትኣበዩ በበይናቲሆሙ ከመ ኢትግበሩ ዘትፈቅዱ፤ ወባሕቱ እብለክሙ በመንፈስ ሑሩ ወፍትወተ ሥጋክሙ ኢትግበሩ፣ማለትም ሥጋ መንፈስ የማይወደውን ይወዳል፤ መንፈስም ሥጋ የማይወደውን ይወዳል፤ እርስ በርሳቸውም ይቀዋወማሉ፤ስለዚህም የምትወዱትን ልታደርጉ ኣትችሉም፤ ነገር ግን እላለሁ በመንፈስ ተመላለሱ የሥጋን ምኞት ግን ከቶ ኣትፈጽሙ››(ገላ.፭÷፲፮‐፲፰)፡፡
እነኝህ የውስጣችን ጠባዮች በዚህ ደረጃ እርስ በርስ የሚቃረኑ መሆናቸው ለምናስተውላቸው በግልጽ የሚታወቁ ናቸው፤ ከዚህ አንጻር ሰይጣን ይህንን ክፍተት ተጠቅሞ የሥጋችንን ፍላጎት እንድንከተል ይገፋፋናል፤ መሳሪያዎቹ ደግሞ ፍቅረ መባልዕት፣ ፍቅረ ንዋይና ፍቅረ ሢመት ናቸው፤ ይህም በመሆኑ ነው ሰይጣን፣ በነዚህ ጌታችንን ሊሸነግለው የሞከረ፤ይሁንና ጌታችን እነኝህን የሽንገላ መሣሪያዎች ሰባብሮ ጥሎኣቸዋል፤የጣላቸውም በጾምና በእግዚአብሔር ቃል ነው፤
ጾም መጾም ማለት ከፍቅረ መባልዕት፣ ከፍቅረ ንዋይና ከፍቅረ ሢመት ፍላጎት ጨርሶ መራቅ ማለት ነው፤ ይህንን ኣደረግን ማለት ደግሞ ሥጋችን የማይወደውን፣መንፈሳችን ግን የሚወደውን ነገር ኣደረግን ማለት ነው፤ ይህ ሲሆን ሰይጣን ከሰረ፤ ድልም ሆነ ማለት ነው፤ በዚህ መንፈሳዊ ኃይል ዲያብሎስ ተሸንፎና ተስፋ ቆርጦ ይሄዳል፡፡
ከዚህ ኣኳያ እኛም በቃለ እግዚአብሔር እየተመራን የምንጾምበት ምክንያት የሥጋችንን ፍላጎት በመግራት ለነፍሳችን ፍላጎት ለማደርና በዚህ ኃይለ መንፈስ ሰይጣንን በማሸነፍ የእግዚአብሔር ቤተ ሰብ ለመሆን ነው፡፡
የተከበራችሁ ሕዝበ ክርስቲያን ልጆቻችን!
የጾም ዋና ዓላማ ሥጋዊ ፍላጎትን መግራት፣ በምትኩ ደግሞ መንፈሳዊ ፍላጎትን ማጐልበት እንደሆነ ተነግሮናል፤ በመሆኑም ይህንን መርሕ ጠብቀን መጾም ግዴታችን ይሆናል፤ ዛሬ ባለንበት ዓለም ሥጋዊ ፍላጎታችን ያየለበት፣መንፈሳዊ ፍላጎታችን ግን የተዳከመበት ዘመን ላይ እንገኛለን፤ ከፍቅር ይልቅ ጥላቻ፣ ከኣንድነት ይልቅ መለያየት፣ ከመራራት ይልቅ ጭካኔ፣ ከእምነት ይልቅ ክሕደትና ኣስመሳይነት በዓለማችን ላይ የበላይነቱን ይዞ መገኘቱ ለዚህ ማሳያ ነው፡፡
ይሁንና ዓለም ቢሰማም ባይሰማም፣ ሓቁም ጠቃሚውም የመንፈስን ፍላጎት ማጐልበት ስለሆነ የመንፈስ ፍሬዎች የሆኑትን ማለትም፣ ፍቅርን ሰላምን፣ ኣንድነትን፣ ርኅራኄንና፣ ሃይማኖትን፣ ማስፈን ምርጫችን ልናደርግ ይገባል፤ ቤተክርስቲያንም እንድንጾም የምታስተምረን እነዚህን ለመተግበር ጾም ፍቱን መሳሪያ ሆኖ ስለሚገኝ ነው፡፡
ከዚህ አንጻር የጾም ዓላማውና ግቡ ጽኑዕ ሃይማኖትን፣ እውነተኛ ፍቅርን፣ ዘላቂ ሰላምን፣ ልባዊ ኣንድነትን፣ የማይናወጽ ፍትሕንና እኩልነትን፣ ወሰን የሌለው ርኅራኄን በውስጣችን፣ ብሎም በዓለማችን ማሥረጽ እንደሆነ በውል ተገንዝበን ጾሙን መጾም ይገባል፤ልንለብሳቸው የሚገቡ እነዚህ የመንፈስ ፍሬዎች የእግዚአብሔር ጋሻዎች ናቸውና፡፡ ይህንን ካደረግን እንደ ጌታችን የሰይጣንን ሽንገላ በጣጥሰን በመጣል በኣስተማማኝ ሁኔታ ድል ማድረግ እንችላለን፤ የተጠራነውም ለዚሁ ነው፡፡
በመጨረሻም፡-
የሕዝባችንና የሀገራችን የራስ ምታት ሆኖ የሚገኘውን ያለመግባባት ዝንባሌ ለመቅረፍ ከልብ በመጸለይ፣ እንደዚሁም የተራቡትን በማጒረስ፣ የታረዙትን በማልበስ፣ የተጠሙትን በማጠጣት፣ የተጣሉትን በማስታረቅ፣ ፍትሕ ለተነፈጉትም እውነተኛ ፍትሕን በመስጠት፣ መዋዕለ ጾሙን እንድንጾመው በእግዚአብሔር ስም ኣባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን።
“እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ”

ወስብሓት ለእግዚአብሔር አሜን!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ
ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፡፡


የካቲት ፱ ቀን ፳፻፲፰
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ
#ተዋሕዶ #ኦርቶዶክሳዊ #መዝሙር

14/02/2026

#ተዋሕዶ #ኦርቶዶክሳዊ #መዝሙር

ስጋ ስጠኝ እባክህ ቅንጥብጣቢም ቢሆን ስለ ማርያም አሉ የሆኑ መለኩሴ ስጋ ቤቴ መስኮት ላይ ቆመው....በስራ ተጠምጄ ስለነበር "እግዚአብሔር ይስጥልኝ"ብዬ ብቻ ፊት ነሳኋቸው። እሳቸው ግን አ...
14/02/2026

ስጋ ስጠኝ እባክህ ቅንጥብጣቢም ቢሆን ስለ ማርያም አሉ የሆኑ መለኩሴ ስጋ ቤቴ መስኮት ላይ ቆመው....በስራ ተጠምጄ ስለነበር "እግዚአብሔር ይስጥልኝ"ብዬ ብቻ ፊት ነሳኋቸው። እሳቸው ግን አላቆሙም

ስለ ማርያም ልጄ ..ስለ ፈጠረህ ..ትንሽ ቁራጭ ስጋ ትንሽ ብቻ...

ጭራሽ ደሜ ፈላ!!!ስጋውን ጥሎ ስሜቱን ንቆ ሆዱን ረስቶ ገዳም የገባ ቆብ የደፋ መለኩሴ ለስጋ ሲንገበገብ ሳይ ....

ቆይ መለኩሴ አደሉ??ቆሎ አይበሉም??ምን ስጋ ቤት ለስጋቤት ያዞሮታል???ለሀገር አይፀልዩም ???ያው እንኩ ሂዱልኝ ...ብዬ ከስጋ ላይ ገፍፌ ያነሳሁትን ሞራ እና ቅንጥብጣቢ ስጋ ወረወርኩባቸው።ወድያ ፈገግ ብለው የምርቃት መአት አዝንበውብኝ ሄዱ...አሜን እንኳን አላልኩም ሆዳም ቄስ መረቀኝ ረገመኝ እያልኩ ስራዬን እንደቀጠልኩ ቀና ስል መለኩሴው መንገድ ተሻግረው ለእርጉዝ የኔ ቢጤ ደናውን እየመረጡ ሲያጎርሷት አየሁና ፈጥኜ ወጥቼ መለኩሴውና ሴትየዋ አጠገብ ደረስኩ....የምለው ግን ጠፍቶኝ ነበር

ምነው አባ ለነብሰ ጡር ነው ቢሉኝ እኔኮ....

ተው ልጄ ደግነትኮ ሰው አይመርጥም ግን ይህንንም ማድረግህ ጥሩ ሰው ነህ

ማለት አባ ይሄንን የሚጣል ስጋ ሰጥቼዎት እንዴት እንዲህ ይሉኛል

ልጄ አንተጋ ከመድረሴ ብዙ ጠይቄ ሰድበው አባረውኛል ሆዳሙ መለኩሴ ብለውኛል።chachaእቺ ሴት ነብሰ ጡር ናት በዛላይ የኔ ቢጤ ከቤተክርስትያን ኪዳን አድርሼ ስመለስ ለፆም መያዣ ሰወች በፔስታል ስጋ ይዘው ሲያልፉ አይታ አማረኝ አለች የነብሰጡር አምሮት ደሀ ሀብታም አይልም እንዳልገዛላት እኔም ምስኪን ነኝ ሰው ሁሉ ስጋ ስለምን ሲያየኝ በኔ ፈርዶ ነበር አንተ ግን ቅንጥብጣቢም ቢሆን ሰጠከኝ

አይ አይ በፍፁም እኔ መጥፎ ጨካኝ ሰው ነኝ ይቅር በሉኝ አባቴ

እሱ ይቅር ይበልህ ልጄ ዘንድሮ ስጋ ቆራጩ በዝቷል ግን ስጋውን ሚቆርጠው ለገዛ ለስጋው ነው።
Chacha ስጋ ለነብስ ሲቆረጥ ነበር ጥሩ...."አየህ እኔ ካህን ነኝ ስጋ አያምረኝም ሁሌ እበላለሁ ደሞ የኔ ስጋ አንዴ በልተውት የማያስርብ የክርስቶስ ስጋ ነው አንተስ ከበሬ ስጋ ቆራጭነት ወደ ክርስቶስ የከበረ ስጋ እና ደም ተቀባይነት ምትሸጋገረው መቼ ነው

አይ አባቴ እንጃ የኔማ ነገር

እንግዲህ አስተውል ዛሬ የምትሸጠው ስጋ ትላንት በሬው በነብስ ነበር...አሁን ስጋ ብቻ ሆኗል።የሆነ ቀን እኛም ነበርን ተብለን ጠዋቱን ሬሳ ብቻ እንሆናለን...በቅበላ ሞትን እንቅደመው ልጄ አሉኝ
Chacha እሺ አልኩ እሺታዬ የልብ ነበር ያቺን ምስኪን ነብሰጡር ቤቴ ወስጄ ጋበዝኳት ሲነጋልኝ በጠዋት እግዚአብሔር ቢፈቅድ ከፆሙ ጋ የነብሴን ጌታ እኔም እቀበለዋለሁ።
©:cha cha and EOTC

ዐቢይ ጾም (ጾመ ፵ ዘጾመ ክርስቶስ)በመ/ር ጌታቸው በቀለይህ ጾም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ ፵ መዓልትና ሌሊት ከቆመ ሳያርፍ፣ ከዘረጋ ሳይጥፍ  በትኅርምት የጾመው...
14/02/2026

ዐቢይ ጾም (ጾመ ፵ ዘጾመ ክርስቶስ)
በመ/ር ጌታቸው በቀለ
ይህ ጾም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ ፵ መዓልትና ሌሊት ከቆመ ሳያርፍ፣ ከዘረጋ ሳይጥፍ በትኅርምት የጾመው ጾም በመሆኑ “ዐቢይ ጾም” ተብሏል /ማቴ. ፬፥፬/፡፡ እኛም ጌታ የጾመውን ለማስታወስ፣ በረከቱን ለማግኘት፣ በግብር እርሱን ለመምሰል፣ የሥጋ ፈቃዳችንን ለነፍስ ፈቃዳችን ለማስገዛት እንጾመዋለን፡፡ ጌታችን የጾመው እቀደስ፣ እከብር ወይም እነጻ ብሎ ሳይሆን ለእኛ አርአያ ለመሆን ነው፡፡ ዐቢይ ጾም ከሰባቱ የዐዋጅ አጽዋማት አንዱ ነው፡፡
የዐቢይ ጾም ስምንት ሣምንታት
ቅዱስ ያሬድ በጾመ ድጓው በዐቢይ ጾም ለሚገኙት ሰንበታት ሁሉ የተለየ መዝሙር ሠርቶላቸዋል፡፡ ሰንበታቱም በመዝሙሩ ስም፡-
፩- ዘወረደ
፪- ቅድስት
፫- ምኩራብ
፬- መጻጉዕ
፭- ደብረ ዘይት
፮- ገብርኄር
፯- ኒቆዲሞስ
፰- ሆሣዕና ተብለው ይጠራሉ፡፡ /መጽሐፈ ድጓ/፡፡

የበረከትና የዕረፍት ዕለታት በመሆናቸው ከሥጋ ሐሳብና ሥራ ተለይተን በእግዚአብሔር ቃል በጸሎትና በዝማሬ ተግተን ለእግዚአብሔር ምስጋና የምናቀርብባቸው ናቸው፡፡ ዐቢይ ጾም ስምንት ሳምንታት (፶፭ ቀኖች) አሉት፡፡
በስምንቱ ሣምንታት ውስጥ ስምንት ቅዳሜዎች፣ ሰባት እሑዶች ይገኛሉ፡፡ ይኸውም ዐሥራ አምስት ቀን ማለት ነው፡፡ እነዚህ ቀናት ከጥሉላት እንጂ ከእህል ውኃ ስለማይጾሙ የጾሙ ወራት ዐርባ ቀን ብቻ ይሆናል፡፡
የዐቢይ ጾም ሥያሜዎች
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በዐዋጅ ከሚጾሙት ሰባቱ አጽዋማት አንዱና ትልቁ ዐቢይ ጾም ይባላል፡፡ ይህ ጾም በተለያዩ ሥያሜዎች ይታወቃል፡፡ የይኸውም፡- ዐቢይ ጾም፣ ጾመ ኢየሱስ፣ ጾመ ሁዳዴ፣ ዐርባ ጾም በመባል ይታወቃል ፡፡ እነዚህንም እንደሚከተለው እንመለከታቸዋለን፡-

ዐቢይ ጾም
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ የጾመው ጾም ስለሆነ “ዐቢይ ጾም” ይባላል፡፡
ጾመ ሁዳዴ
በጥንት ዘመን ገባሮች ለባለርስቱ የሚያርሱት መሬት “ሁዳድ” ይባል እንደነበር ዐቢይ ጾምም ሠራኤ ሕግ ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመውና ምእመናን ይህን እያሰቡ ከልሒቅ እስከ ደቂቅ የሚጾሙት ስለሆነ “ጾመ ሁዳዴ” ይባላል፡፡
የካሣ ጾም
የቀድሞዎቹ ሰዎች አትብሉ የተባሉትን በመብላታቸው ከገነት ለመባረር ለውርደትና ለሞት ለሲዖል ባርነት ተዳርገዋል፡፡ ዳግማዊ አዳም የተባለ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን በሆድ ምክንያት ድቀት አግኝቶት ረኃበ ጸጋ ደርሶበት የነበረውን ቀዳማዊ አዳምንና ልጆቹን በፈቃዱ በጾመው ጾም ካሠን፡፡ ስለዚህ ዐቢይ ጾም “የካሣ ጾም” ይባላል፡፡
የድል ጾም
አዳምና ሔዋን በገነት ሳሉ በምክረ ከይሲ ተታለሉና ድል ሆኑ፤ ተስፋ አበውን ሊፈጽም የመጣ ክርስቶስም ዲያብሎስን ድል ያደርግልን ዘንድ ተጠምቆ ሳይውል፣ ሳያድር ከዚህ ዓለም ርቆ ወደ ገዳም በመሄድና ከሰው ተለይቶ ፵ መዓልትና ሌሊት በመጾም ዲያብሎስን፣ ፈቃደ ሥጋችንን ድል የምናደርግበትን ኃይል አጎናጸፈን፤ ስለዚህ ዐቢይ ጾም ሦስቱ አርእስተ ኃጣውእ ድል የተነሡበት ዲያብሎስ ያፈረበት ስለሆነ “የድል ጾም” ይባላል፡፡
የመሸጋገሪያ ጾም
ነቢዩ ሙሴ ፵ ቀንና ሌሊት በሲና ተራራ ጾሞ እሥራኤል ዘሥጋን ከሕገ ልቡና ወደ ሕገ ኦሪት ያሸጋገረ ሲሆን፤ ክርስቶስም እሥራኤል ዘነፍስ የተባልነውን ከሕገ ኦሪት ወደ ሕገ ወንጌል ፵ መዓልትና ሌሊት በመጾም ያሸጋገረን በመሆኑም “የመሸጋገሪያ ጾም” ተብሎ ይጠራል፡፡
ጾም አስተምህሮ
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያለ ድካም ሁሉን ማድረግ ሲቻለው መምህረ ትሕትና ነውና አርአያውን ሊተውልን ራሱን ዝቅ አደረገ፡፡ እኛን ወደ እርሱ በፍቅረ ይስበን ዘንድ አስቀድሞ ወደ እኛ መጣ፡፡ መጥቶም ረኃባችንን ተራበ፣ ድካማችንን ደከመ፣ ፈተናችንን ተፈተነ፡፡ ስለዚህ በጾሙ ትሕትናን ትዕግሥትንና ድል ማድረግን ስላስተማረበት ጾሙ “ጾመ አስተምህሮ” ይባላል፡፡
ቀድሶተ ገዳም
እነ ዮሐንስ፣ እነ ኤልያስ የኖሩትን የብትሕውና ኑሮ ለባሕታውያን፣ ለመነኮሳት ባርኮ ስለ ሰጠ፤ ከከተማ ርቆ ከሰው ተለይቶ በገዳም ከአራዊት ጋር ኖሮ በዲያብሎስ ተፈትኖ ድል አድርጓልና ጾሙ “የቀድሶተ ገዳም ጾም” ይባላል፡፡
የሥራ መጀመሪያ ጾም
ጌታችን የማስተማር ሥራውን ከመጀመሩ፣ አንቀጸ መንግሥተ ሰማያትን ከማስተማሩ አስቀድሞ የጾመው በመሆኑም “የሥራ መጀመሪያ ጾም” ተብሎ ይጠራል፡፡ ስለሆነም ሐዋርያት እርሱን አብነት አድርገው ሠራቸውን በጾም ጀመሩ፡፡
እንደ ማጠቃለያ
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን ጾም የጾመው ለአብነት፣ ለማስተማር፣ ለአርዓያ ነው። በዚህ ታላቅ ጾም ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ፣ ከሰው የሥጋ ጠባይ የሚመጣ ስስትና ፍቅረ ንዋይ ድል የተነሱበት ነው። እኛም ይህን እያሰብን በተለያየ መንገድ የሚመጣብንን ፈተና ለማራቅ ከዚህ ታላቅ ጾም በረከት እንድናገኝ እንጾማለን። ጸልዮ ጸልዩ፣ ጾሞ ጹሙ ብሎናል። /ማቴ.፮፥፲፮/። ጾም ለክርስቲያኖች ዲያብሎስን ድል የምንነሣበት መንፈሳዊ የጦር ዕቃ ነው። ስለዚህ ሐዋርያዊትና ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን እንደምታስተምረን ይህን ጾም ከምግብ ለመከልከል ጋር ጸሎትን፥ ስግደትን፣ ምጽዋትንና የንስሐ ዕንባን ጨምረን እንጹመው።

ጌታችንና ነቢያት፣ ሐዋርያት የተውልን መንፈሳዊ መሣሪያ ነውና፡፡ እንግዲህ ዐብይ ጾም ማለት ጌታ ስለኛ ባየው መከራ የምናዝንበት፣ በሰጠን ኃይል ከሰይጣንና ከፈቃደ ስጋ የምንዋጋበት፣ በበደልነው ገብቶ የካሠልንን እያሰብን ዳግም ወደ ኃጢአት ላንመለስ ቃል የምንገባበት፤ አርአያ ሆኖ ከሠራልን ሥርዐት፤ ከኖረልን ሕይወት የምንማርበት፤ ራሳችንን ለፋሲካው በግ ለሥጋ ወደሙ የምናዘጋጅበት ሰሞን ነው፡፡ በመሆኑም በሰላም፣ በፍቅር፣ በትሕትና ጾመን ለበዓለ ትንሣኤው በሰላም እንዲያደርሰን፣ ጾመን ለማክበር እንዲያበቃን እግዚአብሔር በቸርነቱ ይጠብቀን፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን የበረከት ጾም ያድርግልን፡፡ አሜን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ዋቤ መጻሕፍት፡-
✍️ መጽሐፍ ቅዱስ
✍️ ፍትሐ ነገሥት
✍️ መጽሐፈ ድጓ
✍️ ሃይማኖት አበው
✍️ ስንክሳር
✍️ የቤተክርስቲያን ታሪክ በኢትዮጵያ
✍️ በዓላት
✍️ ጾም፣ ጸሎት ምጽዋት
✍️ Enclopedia of Aethiopica
©:EOTC TV

14/02/2026

#ተዋሕዶ #ኦርቶዶክሳዊ #መዝሙር

12/02/2026

#ተዋሕዶ #ኦርቶዶክሳዊ #መዝሙር

Address

Haile Gebresilassei Road
Addis Ababa
1000

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Keranio Media ቀራኒዮ ሚዲያ posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Organization

Send a message to Keranio Media ቀራኒዮ ሚዲያ:

Share