06/01/2024
የገና ጨዋታ
(በካህሳይ ገ/እግዚያብሄር)
የገና ጨዋታ በአገራችን መዘውተር የጀመረው ከጌታ ልደት በኋላ ጀምሮ እንደሆነ ነው የሚነገረው፡፡ ጨዋታው በዚህ ዘመንና ዓ.ም ተጀመረ የሚል የጽሑፍ ማስረጃ ባይገኝም በጥንታውያን ገዳማት በሚገኙ የግድግዳና ብራና መጻሕፍት ከጌታ ልደት ሥዕል ጐን ሕፃናት የገና ጨዋታ ሲጫወቱ የሚያሳዩ ሥዕሎች መኖራቸው ሲታይ ጨዋታው በሺሕ ለሚቆጠሩ ዓመታት ሲዘወተር ለመቆየቱ ተጨባጭ ማሳያ ነው፡፡
የገና ጨዋታ እንዴትና ለምን ተጀመረ ለሚለው ጥያቄ በትውፊታዊ ታሪኮች ላይ የተመሠረቱ ሁለት ምላሾች አሉ፡፡ አንደኛው የገና ጨዋታ በሰብአ ሰገል ሰራዊት አማካኝነት ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣቱ በፊት በቤተልሔም ከተማና በአካባቢው የተለመደ ጨዋታ ነበር፤ የተለየ ነገር የሆነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደበት ዕለት መልአኩ የምሥራቹን ለእረኞች ነግሯቸው የጌታን መወለድ በዓይናቸው ዓይተው፣ ከሰማይ መላእክት ጋር የሰላም መዝሙር ከዘመሩ በኋላ በደስታ የገና ጨዋታ ተጫውተዋል የሚለው ነው፡፡ ጌታችን የተወለደው ንጉሥ ባዜን ኢትዮጵያን ይገዛ በነበረበት ዘመን ነበር፡፡ በወቅቱ የጌታን ልደት የምሥራች በዓል ለመካፈል በኮከብ እየተመሩ ወደ ቤተልሄም ከሄዱት አንዱ የንጉሥ ባዜን ወንድም መለኸ እንደነበር ታውቋል፡፡
የገና አጨዋወት አጀማመርን በተመለከተ የሚቀርበው ሁለተኛው ትውፊታዊ ታሪክ ደግሞ የሚከተለው ነው፡፡ በኮከብ (በቅዱስ ገብርኤል) መሪነት ወደ ቤተልሔም የተጓዙት ሦስት የምሥራቅ ነገሥታት እያንዳንዳቸው አንድ መቶ ሠራዊት አስከትለው ነበር የሄዱት፡፡ በወቅቱ ኢየሩሳሌምንና አካባቢውን ይገዛ የነበረው ንጉሥ ሄሮድስ የእነዚህን ነገሥታት መምጣት በመረጃ ደርሶበት ነበርና እንቅስቃሴያቸውን ለመከታተል ይችል ዘንድ ከሰላዮቹ አንዱን የእነዚህ ነገሥታት ወታደሮች አስመስሎ ከመካከላቸው አስገባ፡፡ ይሁንና ሰላዩ ከሰብአ ሰገል ወታደሮች መካከል ሠርጎ እንደገባ ካሰቡበት ቦታ ሳይደርሱ ይመራቸው
የነበረው ኮከብ አልንቀሳቀስም ብሎ ቆመ፡፡ በዚህን ጊዜ ነገሥታቱ እስቲ ሁላችንም ሰዎቻችንን እንቆጣጠር ብለው ሲቆጣጠሩ ሰላዩ ተገኘና አንገቱ ተቀልቶ እንዲሞት ተደረገ፡፡ በዚህን ጊዜ ታድያ ወታደሮቹ የተቀላውን የሰላዩን ጭንቅላት በዱላ እየተቀባበሉ ይጫወቱበት ጀምር፡፡ ይህንን መነሻ
በማድረግ ከዛን ጊዜ ጀምሮ የገና ጨዋታ ተጀመረ፡፡
የገና ጨዋታ ሥርዓትና ባህል
የዛሬን አያድርገውና የመሬት ጥበት ባልነበረበት ጊዜ ለገና መጫወቻ ተብሎ በየመንደሩ ተከልሎ የሚቀመጥ ሜዳ ነበር፡፡ ይህ ሜዳ ከገና መጫወቻነቱ ባሻገር ለከብቶች የግጦሽ መስክ በመሆንም ያገልግላል፡፡ የገና መጫወቻ ሜዳ (መለጊያ) ስፋት ግን ውስን አይደለም፡፡ ቢሆንም እያንዳንዱ ሜዳ የራሱ የሆነ ወሰንና ድንበር አለው፡፡ ይህ መስመር ማለብ ይባላል፡፡ በመሆኑም በጨዋታ ጊዜ ዕሩርዋ ወይም ጥንግዋ የማለቡን መስመር አልፋ መውጣት የለባትም፡፡ ዕሩርና ጥንግ አገልግሎታቸው አንድ ዓይነት ቢሆንም አሠራራቸው ይለያያሉ፤
ሀ. ዕሩር በአብዛኛው ከክትክታ ሥር ከሚገኘው ጉጥ ተቆርጣና ተስተካክላ የምትዘጋጅ ናት፡፡ ሩርዋ በይበልጥ እንድትጠነክር ሲባል በእሳት እንድትለበለብ ይደረጋል፡፡ ዕሩር የሚለው ቃልም በእሳት ያረረ መሆኑን ለማሳየት የተነገረ ነው፡፡
ለ. ጥንግ በአንጻሩ ከበሬ ቆዳ (ጠፍር) በዚህ ሞያ ባላቸው ሰዎች የምትሠራ የገና ኳስ ናት፡፡ አንዳንዴ ዕሩርዋም ሰውን
እንዳትጎዳ ሲባል በቆዳ እንድትሸፈን ይደረጋል፡፡
ዕሩር ከተወሰኑ የዛፍ ዓይነቶች እንደምትዘጋጅ ሁሉ የመምቻ ዱላውም (ቀልባሳ በትር ከተመረጡ የዛፍ ዓይነቶች ነው የሚሰናዳው፡፡ (በነገራችን ላይ የገና መምቻ ዱላው ማጠንጊያ ወይም ጥርባዳ እየተባለ ነው የሚጠራው፡፡)
ለጥርባዳ (ማጠንጊያ) ተመራጭ ከሆኑ የዛፍ ዓይነቶች መካከል ቀረጽ፣ አጣጥ፣ ብሳና፣ ጨባ በዋናነት ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ከእነዚህ የዛፍ ዓይነቶች የሚገኝ ዱላ በክብደቱ ቀላል ነገር ግን ደግሞ በቀላሉ የማይሰበር ነው፡፡ ዱላው የዚህ ዓይነት መሆኑ በጨዋታ መካከል በስህተት በሰውነት ላይ ቢያርፍ የሚደርሰው ጉዳት አነስተኛ እንዲሆን ይረዳል፡፡ ይሁንና በአንዳንድ አካባቢዎች ለገና ዱላ የሚመረጡት የወይራና የክትክታ ዛፎች ናቸው፡፡ ከጨዋታ ጊዜ ውጭ ባለው ጊዜ ዕሩርዋ (ጥንግዋ) በቤተ ክርስቲያን ዕቃ ቤት እንድትቀመጥ ትደረጋለች፡፡
የገና ጨዋታ የሚከናወነው ከልደት እስከ ጥምቀት ባለው ጊዜ ነው፡፡ በበዓለ ልደት ከቅዳሴ በኋላ ዕሩርዋ ከተቀመጠችበት ቦታ ወጥታ በዕለቱ እንዲያጫውቱ ለተመረጡ የቡድን አባቶች (ዳኞች) ትሰጣለች፡፡ ብዙውን ጊዜ የገና ጨዋታ የሚከናወነው በተለይ በመጀመሪያው ዕለት) ከሰዓት በኋላ ነው፡፡ ምክንያቱም ጠዋት ሰው ከቤተ ክርስቲያን መልስ ወደ የቤቱ በመሄድ ለበዓሉ የተዘጋጀውን ድግስ ከቤተሰቡና ከጎረቤት ጋር እየበላ እየጠጣ ስለሚያልፍ ነው፡፡
ወደ ጨዋታው ሂደት ስንመልስ ጨዋታውን መርቀው ዕሩርዋን (ጥንግዋ) ለግተው የሚያስጀምሩት ሁለት የቡድን አባቶች ናቸው፡፡ በዘመናዊ የእግር፣ የእጅና የቅርጫት ኳስ ጨዋታዎች ተፎካካሪ ቡድኖች የየራሳው የሆነ ቋሚ ስም ይኖራቸዋል፡፡ በአገራችን የገና ጨዋታ ሥርዓት ግን ሁለቱም ተፎካካሪ ቡድኖች መጠሪያ ስም የሚሰጣቸው ጨዋታው ሊጀመር ሲል ነው፡፡ በዚህን ጊዜ ሁለት የቡድን አባቶች ከየቡድኑ አንዳንድ የቡድን መሪዎችን (አምበሎች) ይጠሩና ሁለት ስያሜዎችን በማቅረብ በፈቃደኝነት የየራሳቸው እንዲመርጡ ያደርጋሉ፡፡
በዚህ ስምምነት ከሌለ የቡድን አባቶች በዕጣ ስም ያወጡላቸዋል፡፡ በአመዛኙ በአገራችን ለገና ጨዋታ ለቡድን ስም መጠርያነት በአማራጭነት የሚቀርቡት ከአንበሳ ከነብር፣ ከእንጀራ ከጠላ፣ ከገደል ከሾተል የሚሉና የመሳሰሉት ናቸው፡፡
በጨዋታው ወቅት ተመልካቹ በልቶ ጠጥቶ የሚመጣ ቢሆንም ተጫዋቾቹ ግን ከጨዋታ በፊት በጣም በትንሹ መጥነው ነው የሚበሉት፡፡ ይህም እንደልባቸው መሮጥና መንቀሳቀስ ይችሉ ዘንድ ነው፡፡ ካልሆነ ግን እስኪጠግብ በልቶ መጥቶ መሮጥ አቅቶት የተሸነፈ ጊዜ አሸናፊው ወገን፡-
እየው አካሄዱን አረማመዱን፣
እንደ ቃሪያ ሎሚ ወጥሮ ሆዱን፡፡
ትናንት ማታ የበላው ሽልጦ፣
አላስሮጠው አለ ከጐኑ ተሸጦ፡፡
በማለት ይሳለቅበታል፡፡
ይቀጥላል .....
#ዓኢ