07/04/2026
ክፍለ-2
በቃላቸዉ መሰረት ወዲያዉኑ ጌራ ወደ ደቡብ አስቦም ወደ ሰሜን ጫፍ በመሄድ ሰፈሩ፡፡የዉድድር ዝግጅቱ ቀጠለ፤ቅልብ ፈረሶቻቸዉን ጓሳዉ ዉስጥ በመልቀቅ እንዲግጡ ተደረጉ፡፡ከጓሳዉ ወደ ቤታቸዉ ሲመለሱ የገብስ ጥሬ እየተሰጣቸዉ ሲቀለቡ ቆዩ፡፡ፈረሶቹ በድሎት ከመቀለባቸዉ የተነሳ ጥጋበኛ በመሆናቸዉ ለጅብ እንኳ የማይቀመሱ ጥጋበኛ ቅልቦች ሆኑ፡፡ፈረሶቹ አልፎ አልፎ ለማሟሟቅ ሲጋልቧቸዉ ልጓም የማይገዛቸዉ አልንጋ የማያርፍባቸዉ ሽምጥ ሯጭ ሆኑ፡፡በዚህ መሰረት ጌራ እና አስቦ በአረፋበት ሆነዉ የሚጋልቡበትን መንገድ ሲያጠኑና ሲመረምሩ ፈረሶቻቸዉን ገብስ ሲቀልቡ ሰነበቱ፡፡
ቀኑም ደረሰ ጌራ ከደቡብ አስቦም ከሰሜን ጫፍ ፈረሶቻቸዉን ጎህ ሳይቀድ ጭነዉ የፀሐይ መዉጫ ላይ አይኖቻዉን ተክለዉ መጠባበቅ ያዙ፡፡ትልቅ ዉድድር ትልቅ ፋክክር የርስት ማሰከበር ጉዳይ ቢሆንም ያለፊሽካ ያለሩጫ ማሰጀመሪያ ሽጉጥ ያለመነሻ መስመር ያለዳኛ በእምነት ብቻ ዝም ብለዉ የፀሐይቱን መዉጣት መጠባባቅ ጀመሩ፡፡ተፈጥሮ ኡደቱን አይስትምና ፀሐይቱ የእሳት አለሎ መስላ በምስራቅ የተራሮች አናት መሐል ዉስጥ ስትወጣ አስቦ በጥቁር ቦራ ፈረሱ ጌራ በጥርኝ ፈረሱ ላይ ወጥተዉ መጋለብ ጀመሩ፡፡ፈረሶቻቸዉ ቁጥቋጦዉን ጉድባዉን ጥሻዉን እየዘለሉ ሲጋልቡ አርካቡ ላይ ቆመዉ ሰዉነታቸዉን ከፈረሶቻቸዉ ጋር ልክክ አድርገዉ ይሰፋታል ገላጣ ሜዳ ሲያገኙ ደግሞ የሰዉ ዘር በማይታይበት በዚያ ዘመን ጠፈፍ ባለዉ በህዳር ወር መሬት ላይ እንዲህ እያለ ይፎክራሉ
ጌራ፡ የጥርኝ ጌታ ጌራ ቀጭኑ
ጉዳዩ አይደለም ጓሳና ደኑ፡፡
እንኳን በልጓም አዝምሮ ገብሱ
ድንበሩ አይቆምም ተኝቶ ነፍሱ እለ ሲጋልብ
አስቦም በበኩሉ እንዲህ ሲል ይፎክራል
ቦራ ፈረሴ አትዘናጋ
ለዘሮቻችን ታሪክ ይወጋ፡፡
የጌራ ወንድም እህል የያዘዉ
በፈረሱ እግር ጓሳዉን ወቃዉ፡፡
እንዲህ እያሉ እየፎከሩ አስቦ እና ጌራ መንገዱን ቋጥኙን እንደ ቋያ እሳት እየገሰገሱ ጉዞዉን ለበለቡት፡፡ጓሳዉ ላይ ያረበበዉ አመዳይ እና ጤዛ እረግፎ የፀሐይ ሙቀት ሰዉነትን ለማፍታታት ሲደርስ ወንድማማቾቹ ከሁለት አቅጣጫ መጥተዉ ዲጃ ወንዝ ወይም ድጃ አፋፍ ተገናኙ፡፡የፈረሶቻቸዉ አፍ ደም የቀላቀለበት አረፋ ይደፍቅ ነበር፡፡ሁለቱም ከፈረሶቻቸዉ ጀርባ ላይ ተፈናጥረዉ እግራቸዉ መሬት ሲነካ አንድ ሆነዉ ተቃቅፈዉ ተሳሳሙ፡፡ ፈረሶቻቸዉ ደግሞ አፍና አፋቸዉን ገጥመዉ በትኩስ ትንፋሻቸዉ ተገፋፉና በፊት የቀኝ እግራቸዉ መሬቱን ድቅ ድቅ በማደረግ ይፍሩት ገቡ፡፡ በዚህ ጊዜ ጌራ የእናቴ ልጅ ይኽ ነገር ከፈጣሪ ነዉ የርስታችን ድንበር ለይተዉ እንስሳቶቹ ምልክት አበጁበት ሲለዉ አሰቦ ፈገግ አለና ጌራን መልሶ አቀፈዉ፡፡ጓሳዉ ተለካ በዚህ መሰረት ለካስ የአስቦ ፈረስ ጉልበቱ ፍጥነቱ የተሻለ ኖሮ የአስቦ ይዞታ ከጌራ ይዞታ በልጥ ብሎ ተገኘ፡፡
አሁን ድረስ የአስቦ ጓሳ በለጥ ይላል ስሙም የአራድማ ጓሳ በመባል ይታወቃል፡፡የጌራ ደግሞ አነስ ይላል፡፡