03/06/2026
ሲዳማ ክልል ወጣቶች ማህበር 7ኛው ሀገራዊ ምርጫ በሰላማዊ፣ ዲሞክራሲያዊ በሆነ ሁኔታ መካሄዱ ለሀገሪቱ የዴሞክራሲ ግንባታ ጉልህ እመርታ ያለው መሆኑን ገለፀ።
የማህበሩ ፕሬዝዳንት ወጣት በቃሉ መሰረት በተላለፈው መልዕክት፣ ምርጫው በሕዝብ ሰፊ ተሳትፎ፣ በሰላማዊ መንፈስ እና በሕግ የበላይነት ተከናውኖ መጠናቀቁ የዴሞክራሲ ባህል እየጎለበተ መምጣቱን የሚያሳይ መሆኑን አስታውቋል።
በመልዕክቱ ውስጥ ወጣቶች በሀገራዊ ጉዳዮች የሚኖራቸውን ሚና በተግባር እያሳዩ መሆናቸውን በመግለጽ፣ የሲዳማ ክልል ወጣቶች ማህበር አባላት ከክልሉ ወጣቶች ፌዴሬሽን ጋር በመቀናጀት በተለያዩ የምርጫ ጣቢያዎች የምርጫ ታዛቢዎችን በማሰማራት ሂደቱን በቅርበት መከታተላቸውን ጠቁመዋል።
በዚህ ተግባር ወጣቶች በምርጫ ሂደት ያላቸውን ንቁ ተሳትፎ፣ ሀገራዊ ኃላፊነት እና ለዴሞክራሲ ያላቸውን ቁርጠኝነት በግልፅ ማሳየታቸው ተገልጿል። የታዛቢዎቹ ተሳትፎም የምርጫ ሂደቱ ግልፅነትና ተዓማኒነት እንዲጠናከር አዎንታዊ አስተዋፅኦ ማበርከቱ ተጠቅሷል።
ፕሬዝዳንቱ በመጨረሻ ወጣቶች በቀጣይም በሰላም ግንባታ፣ በልማት ስራዎች እና በዴሞክራሲያዊ ሂደቶች ውስጥ ንቁ ተሳትፎ በማድረግ የክልሉንና የሀገሪቱን እድገት እንዲያጠናክሩ ጥሪ አቅርበዋል።