11/06/2026
እንኳን ደስ አለን! እንኳን ደስ አላችሁ!
ጋሞ ልማት ማህበር 60 ሰዎችን የመጫን አቅም ያለው "ሀይላሾ" የተሰኘ ዘመናዊ የሞተር ጀልባ ማስገባቱን ገለፀ!
የጋሞ ልማት ማህበር ዋና ስራ አስፈጻሚ ዶ/ር ኢ/ር ማንደፍሮት ዱባለ እንደገለጹት በተቋሙ ስትራተጂክ ዕቅድ የቱሪዝም ተደራሽነትና መስፋፋት ላይ የየብስና የውሃ ላይ የመዳረሻዎችን አገልግሎት ማስፋፋት አንዱ የትኩረት አቅጣጫ መሆኑን ገልጸዋል:: በዚህም ረገድ እየተከናወኑ ከሚገኙ በርካታ ስራዎች አንዱ በአባያ ሃይቅ ላይ የውሃ ትራንስፖርትና መዝናኛ መሆኑን የገለጹት ዋና ስራ አስፈጻሚው ተደራሽነቱን ለማሳደግ 60 ሰዎችን መጫን የሚችል "ሀይላሾ" የተሰኘውን የሞተር ጀልባ ግዢ ፈጽሞ በዛሬው እለት ሰኔ 4/2018 ዓ.ም ማስገባቱን ተናግረዋል::
"ሀይላሾ" የጋሞኛ ቃል ሲሆን ትርጉሙም አዞ ማለት ነው፡፡ ጀልባው ይህንን ስያሜ ያገኘው በምስራቅ አፍሪካ ቀዳም የሆነ አዞ ራንችን ከማስተዋወቅ ባሻገር በአባያ ሀይቅ ከሚገኙ በርካታ የብዝሃ ህይወት መካከል የናይል አዞ ዝርያ በስፋት መገኘቱን ለማሳየት ታስቦ እንደተሰየመ ዶ/ር ኢ/ር ማንደፍሮት ተናግረዋል፡፡ በቀጣይ ተቋሙ በቱሪዝም ዘርፍ የጀመራቸውን አዲስና ነባር መዳረሻዎች ግንባታ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ዶ/ር ኢ/ር ማንደፍሮት ገልጸዋል::
የጋሞ ልማት ማህበር ም/ዋና ሥራ አስፈፃሚና የቢዝነስ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ዳዊት ዳኜ እንደገለጹት ማህበሩ ቱሪስቶችን መሳብ የሚያስችሉ በርካታ አዲስ መዳረሻዎችን በማልማት ለአገልግሎት ዝግጁ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል:: በአባያ ሃይቅ ላይ የሞጬ ደሴት፣ የአርባምንጭ አዞ ራንች እድሳትና አገልግሎት መስፋፋት፣ 40-42/አርባ አርባ አርባ ሁለት/ ደረጃ መንገድ እንዲሁም በአባያ ሃይቅ ላይ የውሃ ላይ ጉዞና መዝናኛ የሚጠቀሱ አዲስ የቱሪዝም መዳረሻዎች መሆናቸውን አቶ ዳዊት ገልጸዋል::
በውሃ ላይ ጉዞና መዝናኛነት አገልግሎት ተደራሽነትን ለመጨመር ተቋሙ ከዚህ ቀደም 30 ሰዎችን መያዝ የሚችል የጀልባ አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ መሆኑን ያወሱት አቶ ዳዊት ተደራሽነቱን ለማስፋት በአሁኑ ወቅት 60 ሰዎች የመጫን አቅም ያለውን ዘመናዊ ጀልባ በግዢ መገዛታቸውን ተናግረዋል::
ጀልባው ወደፊትም ወደ ኋላም ጉዞ ማድረግ የሚችል መሆኑ በአይነቱ ዘመናዊ እንደሚያደርገው የገለጹት አቶ ዳዊት በተጨማሪም ባለ ሁለት ደረጃ ወለሎች ያሉት 48 ሰው ከታችኛው ወለል እና 12 ሰዎችን ከላይኛው ወለል የመጫን አቅም እንዳለው አስታውቀዋል::
በጋሞ ልማት ማህበር የቱሪዝም ልማትና አገልግሎት ኢንተርፕራይ ሥራ አስኪያጅ አቶ ደጉ ደሳለኝ ጋሞ ዞን የበርካታ መስህቦች ባለቤት ሲሆን አበዛኞዎቹ መስህቦች በአግባቡ ያልለሙ በመሆኑ በዞኑ ወስጥ ያሉ ፀጋዎችን ወደ ኢኮኖሚ ለመቀየርና ለአካባቢው ህበረተሰብ የሥራ ዕድል ለመፍጠር ማህበራትቸን እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል:: ዘርፉን ለማሳደግ ሁሉም የዘርፉ ባለድርሻ አካላት ከማህበሩ ጋር ተባብሮ እንዲሰራ አቶ ደጉ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡
ቅድሚያ ለጋራ ልማት!
ሰኔ 4/2018