12/04/2026
“ነፍስህ በሰላም ትረፍ”!
ሁሌም አብሮን ራሱ የሚከብርበትን ታላቅ ነገርን የሚያደርግ እግዚአብሔር ይመስገን።
ፋሲካን እኔና ባለቤቴ ቴዲዪ ከጥቂት የባለ ዐደራ ትውልድ ቤ/ክ ወንድሞችና እህቶች ስድስት ኪሎ አካባቢ የሚገኘው የእማሆይ ቴሬሳ በጎ አድራጎት ድርጅት ተገኝተናል።
በጎ አድራጎት ድርጅቱ በውስጡ ከ300 በላይ የሆኑ ወንዶችና ሴቶች ህሙማንን ይዟል። ከእነርሱም መሃል በጎዳና ላይ ሆነው ያረገዙ ወጣት ሴቶችን እንዲሁም እመጫቶችንም ተመልክተናል።
ጥቂትም ቢሆን ለሞት የሚያጣጥሩ ወንድሞችን አይተን የዘላለም ህይወት ተስፋ የሆነውን ኢየሱስን ነግረናቸዋል። ከገጠመን ያስገረመኝ እያስጎበኘችን የነበረችው ሲስተር ወደ አንድ ለሞት የሚያጣጥር ሰው ወሰደችንና “ይህ ሰው ሰኢድ ይባላል እንደምታዩት ደክሟል እስከ ከሰዓት የሚቆይ አይመስለኝም አለችና ግንባሩ ላይ በጣቷ የመስቀል ምልክት አድርጋ በሰላም እረፍ አለችው” ሲስተሯ ይህን ብላ ከሌሎቹ ወንድሞች ጋር ወጣች እኔና ጥቂት እህቶች በዚያ ቀረን።
በርግጥም እያጣጣረ ይመስላል። በፀሎት ከምትመራን እህት ጋር ተስማምተን ፀሎታችንን ቀጠልን በመጨረሻም ሰአኢድን ለጌታ አደራ ሰጥተን አመስግነን ወደ ሌሎች ታካሚዎች ጋር ሄድን። ሁሉንም አከናውነን ጨርሰን ለመሄድ ስንነሳ ለመጨረሻ ጊዜ ሰኢድን አይተነው ልንወጣ ፈልገን ሄድን ስናየው ተገረምን ምክንያቱም ሰይድ ደህና ሆኖ ማውራት ጀምሮ ነበርና።
ደስ አለን! ጌታ ታማኝ አይደል? ዕድልን ሰጠው። ጌታንም እንዲቀበል ለመንነው አደመጠን ግን መወሰን ሳይችል ቀረ። ነርሷም የሰኢድን ደህና መሆን መስክራ ሌሎች ፀሎት የሚፈልጉ ወገኖች ወዳሉበት መራችን። ጌታ ስራን አበዛልን ደስም አለን።
በተጨማሪም ከጥቂት ታካሚና ነፍሰ-ጡር እህቶች ጋር ጌታን በጊታር አመለክን፣ ወንጌልንም አበሰርን ጌታም ስድስት የሚሆኑም ሰዎች ለራሱ ማረከ። ክብር ለጌታ ይሁን!!
ሌላው በግሌ ያስተዋልኩት በስፍራው በርከት ያሉ ከተለያየ ሀገራት የሆኑ የካቶሊክ እምነት ደናግል እህቶችን እያየሁ እነዚህ በመከራ ውስጥ እያለፉ ያሉትን ወገኖቻችንን በትጋት ሲያገለግሉ፣ ያለስስትና መጠየፍ ሲያቅፉ አልፎም
የማያደላ ፍቅርን ሲሰጡ አስተውያለሁ። ለደናግሎቹ ህይወት ይሄው ነው።
በዚህች የምታጓጓ በምትመስል ከንቱ ዓለም ላይ ሁሉን ንቀው ወጣትነታቸውን ለዚህ በጎ ዓላማ ሰውተው ይኖራሉ። ቀናሁ! ህይወቴ እንዲህ በሆነም ብዬ ተመኘሁ!! ሁሌ መልካም መሆን፣ ሁሌም ከችግረኛ ጋር አብሮ ማሳለፍ፣ ሁሌም ከሚያዝኑት ጋር አብሮ ማዘን። በዚህ ሁሉ ውስጥ ደግሞ የዘላለም ህይወት ተስፋ የሆነውን ኢየሱስን መስበክ፣ ማስተዋወቅ።
በአጭሩ,,, ደስ ብሎኝ ያሳለፍኩት በዓል ሆኖልኛል። ጌታን አብዝቼ አመሰግነዋለሁ።
ይህ ውጥኔ እውን እንዲሆን በገንዘብ፣ በዓይነት፣ በፀሎትና በጊዜ አብራችሁኝ የቆማችሁ ወገኖቼ ከልቤ ላመሰግናችሁ እወዳለሁ። እመኑኝ ጌታ ደስ ብሎታል። ይህ በእኛ ሊያደርግ የሚሻው የከበረ ሀሳቡ ነውና! ቡሩክ ሁኑልኝ።
መልካም በዓል