05/06/2025
የማልኮም ኤክስ የሐጅ ምስክርነት እና ገጠመኞች ወደ ቤተሰቡና ጓደኞቹ የተላኩ ደብዳቤዎችና የአመለካከት ለውጥ ጥሪ መልዕክት 🖋 Mohammedawel Hagos
"በነቢይ ኢብራሂምና በነቢይ ሙሐመድ አገር ውስጥ ሆኜ አላህ ዓይኖቼን ከፍቶልኝ ስለ ትክክለኛው የእስልምና ሃይማኖት ተገለጸልኝ፤ በአሜሪካ ያለውም አጠቃላይ የዘርና የቀለም ልዩነት ሁኔታ ጥርት ብሎ ታየኝ"ቀደም ሲል የጥላቻና የኃይለኛነትን ንግግር ሲያደርግላቸው የሚያውቁት ሁሉ ስለ አዲስ አሁን ስላለው አቋሙ ምን ይሉ ይሆን የሚለው ጥያቄ እራሱን አስገረመው። ጥቂት ካሰበበትና "በቃ ሕይወቴ በሙሉ በተለያዩ የለውጥ ሂደቶች የተሞላ ነው፤ ምን አዲስ ነገር አለ?!" ብሎ እራሱ ለራሱ ጥያቄውን መለሰለት።
"አሜሪካ የእስልምና ሃይማኖትን ምንነት መረዳት አለባት፤ ምክንያቱም እስልምና በአንድ ማኅበረሰብ ውስጥ ያለውን የዘርና የቀለም ችግር መንግሎ የሚጥል ሃይማኖት ነው።"
በአሜሪካን አገር ቢሆን "ነጮች" ልንላቸው የምንችላቸውን ሰዎች በአረብ አገሮች ቆይታው አግኝቷል፣ አነጋግሯል፣ አብሮም ቆይቷል። "እነዚህ 'ነጮች' እንኳ ነጭ መሆናቸውን ከውስጣቸው ፈቅደዋል። ይህም የሆነው የእስልምና ሃይማኖት ተከታይ ስለሆኑ ነው። ሌላው ቀርቶ የተለያየ ቀለምና ዘር ባለቤቶች የሆኑ ሆነው ሳለ ያንን ልዩነታቸውን ባለማጠንከር እንዲያውም ከነአካቴው ዘንግተውት ወይም ቦታ ሳይሰጡት ሁሉም በአንድነት ተሰባስበው በፍቅር፣ በደስታና በወንድማማችነትና በእኅትማማችነት መንፈስ ሆነው መመልከቱ እጅግ አስደስቶኛል። እምነታችን በአንድ አምላክ በመሆኑና ሁላችንም በወንድማማችነት ስለምንተያይ የቆዳ ቀለማችንን ምንነት ረስተናል። ቀለም ዋጋ ሊሰጠው የሚገባ ነገርም እንዳልሆነ አውቀናል።"
"እናም ከዚህ ቀደም ያራመድኩትን የጥላቻ ዓይነት ፍልስፍና አሁን ባገኘሁት ግንዛቤ አኳያ አስተካክዬ በአዲስ መልክ አዲስ አስተሳሰብን ማስኬድ አስፈልጎኛል። አዲስ ልምድንና አዲስ እውነትን ተቀብሎ ያለፈውን በማሻሻል ለውጥን ማራመድ ከሰው ልጅ የሚጠበቅ ነገር ነው። ትክክለኛው እውነት ጋር ሲደረስ ደግሞ ያንን የቀድሞውን የተሳሳተ ሁኔታ አሽቀንጥሮ መጣል እጅግ አስፈላጊ ነው።"
የቆዳ ቀለማቸው ከነጭም ነጭ የሆነ፣ የፀጉራቸውም ቀለም ከብሎንድም ብሎንድ ወርቃማ የሆነ፣ እንደዚሁም የዓይኖቻቸው ቀለም ከሰማያዊም በላይ ሰማያዊ ከሆኑ ፈረንጅ አረቦች ጋር አብሮ በልቷል፣ ጠጥቷል፣ አብሮም አንዱን ፈጣሪያችንን አላህን አመስግኗል። "የእነዚህ ነጮች አረቦች ሥነምግባራዊ ሁኔታ፣ የአንደበታቸው ቁጥብነት፣ በጎ አስተሳሰባቸውና ተግባራቸው በናይጀሪያ፣ በሱዳንና በጋና ተዘዋውሬ ካየኋቸው ጥቁር ሙስሊም ወገኖቻችን ጋር በጣም ተመሳሳይ ነ
"እናም ከዚህ ሁኔታ ተነስቼ ስለ አሜሪካ መናገር የምፈልገው ምንድነው ብትሉኝ ነጭ-አሜሪካ የተባለችው አገር የፈጣሪን አንድ መሆን በሙሉ ልቧ መቀበል ይኖርባታል። ይህን ካደረገች ብቻ ነው የሰውን ልጅ አንድ የመሆን እውነት መረዳት የምትችለው። ይህን ካደረገች ደግሞ በቆዳ ቀለም ልዩነት ሳቢያ በሌሎች የአላህ ፍጥረቶች ላይ የምታደርገውን ጥላቻ፣ ጉዳትና ማሰናከል ማቆም ይቻላታል።"
"የቀለም ልዩነትና ዘረኝነት አሜሪካንን የወረረ የማይድን ነቀርሳ መስሎ ሲያጠቃን እያየነው ነው። ክርስቲያን ተብዬዎቹ ነጮች አሜሪካውያን እስካሁን ከተከተሉት አጥፊ ፍልስፍና እውነተኛውንና ለሰው ልጅ እኩልነት በፍቱንነት የሚሰራውን ሃይማኖት ወጥተው መቀበል ይኖርባቸዋል። ይህ ከተደረገ ምናልባትም አሜሪካ ካንዣበበባት ውድመት ለማምለጥ ትችል ይሆናል። አለበለዚያ ግን ልክ ይኸው ዘረኝነቷ ወደ ቁልቁል እንደነዳ እንዳወደማት ጀርመን ትሆናለች።"
በዚች ቅድስት አገር ውስጥ ሆኖ - አሜሪካን አገር በነጮቹና በእኛ በጥቁሮቹ መካከል ስላለው አስከፊ ግንኙነት አወጣለሁ፣ አወርዳለሁ ብሏል። "የአሜሪካን ኔግሮ በፈረንጆች ላይ በጠላትነት ተነሳህ ተብሎ ሊወቀስ አይገባም። ነጮቹ ለአራት መቶ ዓመታት ያደረጉበትንና አሁንም እየተደረገበት ያለውን ግፍ 'አልፈልግም፤ ሁሉ በቃኝ፣ መረረኝ፣ አሻፈረኝ፣ ነፃነት ጠማኝ' ነው ኔግሮው የሚለው። እናም የነጮቹ አሜሪካውያን ምርጫ ትክክለኛው፣ መንፈሳዊውና ሐቀኛው የእስልምና መንገድ መሆን ይኖርበታል።"
"እዚህ በቆይታዬ ሙስሊሞች ቤታቸውን ሰጥተውኝ፣ ምግብ፣ መጠጥ፣ መግዣ፣ እንደዚሁም ሾፌርና ረዳት መድበውልኝ ለአንድ ኔግሮ ሳይሆን ለአንድ ንጉሥ የሚገባውን ክብር ሰጥተው አስተናግደውኛል። 'የዓለሞቹ ሁሉ የበላይ ጌታ ለሆነው ለአላህ ክብርና ምስጋና ይገባው።'"
የናንተዉ
"አል-ሐጅ ማሊክ አል-ሻባዝ" አላህ ይዘንለት 🤲
🖋 Mohammedawel Hagos