19/02/2025
የካቲት ፲፪ የሰማዕታት ቀን!!
ፋሽስት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤ/ክ ላይ ለፈጸመው ጭፍጨፋና ዝርፊያ የኢጣሊያ መንግሥት ይቅርታ ሊጠይቅና ካሣ ሊከፍል ይገባዋል!!
የዛሬው ዕለት የካቲት ፲፪ ቀን (የሰማዕታት ቀን) በኢትዮጵያ በታሪክ የፋሽስቶች ዘረኝነት፣ አውሬያዊ ጭካኔና አረመኔነት በገሃድ የታየበት ቀን ነበር፡፡
በወቅቱ ፋሽሽት በኢትዮጵ ሕዝብ ሕዝብ ላይ ያደረሰውን እጅግ አረመኔያዊ የኾነ ጭካኔና እልቂት በተመለከተ የውጪ ሀገራት ጋዜጠኞችና ታዛቢዎች ከተዉልን የታሪክ ማስታወሻ ጥቂት ሰበዞችን እንምዘዝ እስቲ፤
በወቅቱ በአዲስ አበባ የነበረ አንድ አውሮፓዊ ሐኪም እለቱን እንዲህ ነበር የገለጸው፤
‘‘… ምን ዓይነት አጨካከን ነው፣ ደም በመንገድ ላይ እንደ ውኃ ሲፈስ ያየኹት የዚያን ጊዜ ነው፡፡ የወንዶች፣ የሴቶች፣ የልጆች ሬሳ በያለበት ተኝቷል፡፡ ወዲያው ከባድ የቃጠሎ ጭስ አዲስ አበባን ፅልመት አለበሳት፡፡ የኗሪዎች ቤት ከተፈሸ በኋላ ሰዎቹ በውስጥ እንዳሉ እሳት ተለቀቀባቸው፡፡ ቃጠሎው ቶሎ እንዲያያዝም ቤኒዚንና ዘይት ይጠቀሙ ነበር፡፡ ሰው እሳቱን እየሸሸ ከቤቱ ሲወጣ በመትረየረስ እሩምታ ይገድሉታል፡፡
በዓለም ጦርነት ጊዜ ቁስለኛ ለማንሳት ከግንባር ከቀደመው ጦር ጋር አምቡላንስ ውስጥ እሠራ ነበር፡፡ በሌላም ጦርነቶች ውስጥ ተካፋይ ኾኛለኹ፡፡ በሕይወቴ እንደ አዲስ አበባ ያለ እልቂት ግን አላየሁም፡፡’"
የፋሽስቱ ቤኒቶ ሞሶሎኒ ተወካይ ሩዶልፎ ግራዚያኒ በሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን ላይ የወሰደውን ርምጃ አስመልክቶ በሮማ ላለው ቅኝ ግዛት ሚ/ር መስሪያ ቤት በቁጥር 14-1154 ባስተላለፈው የቴሌግራም መልእክት እንዲህ ነበር ያለው፤
‘‘እነኚህ ጥቁሮች [ኢትዮጵያውያን] የኛን ወታደር ሲያዩ፤ ‹‹ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር! ይላሉ፡፡ ይህን የሚሉትም ለመቀጣጫ እንዲሆኑ ሁሉንም አስጨርስኳቸው፤›› ብሏል፡፡
በዚያው ዘመን እ.ኤ.አ. በየካቲት 22 ቀን የወጣው የሮም ጋዜጣ "ዴል ፖፖሎ"፤ "የአዲስ አበባ አጋማሽ በአሰሳው ጸድቷል፣ 2000 ኢትዮጵያውያን ተይዘው ወደ ደናኔና ወደ ሌሎች ማሰሪያ ቦታዎች ተልከዋል፡፡’" ሲል ዘግቦ ነበር፡፡
ፋሽስቱ ቤኒቶ ሞሶሊኒ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የነበረውን ንቀትና ጥላቻ ያሳየበትና ቢቻለውም ቤተ ክርስቲያኒቱን በፋሽስት ወይም በሮማ አስተዳደር ሥር እንድትሆን የነበረውን ሕልም የሚያጋልጠው እ.ኤ.አ. ታኅሣሥ 16/1935 በአስመራ ለሚገኘው ለጦር አዝማቹ ለማርሻል ባዶሊዮ ያስተላለፈው ጥብቅ ምሥጢራዊ ቴሌግራም እንዲህ ይነበባል፡-
በቁጥር 421M እና በቁጥር 426 ዳግም ያስተላለፍክልኝን የምስጢር ቴሌግራም ደርሶኝ በሚገባ አይቼዋለሁ፡፡ የአክሱም ገዳም ተቀደሰ ሥፍራ እንደመሆኑና ካለውም ጥንታዊ ታሪክና ቅርስ አኳያ በጦር መሣሪያም ሆነ በማናቸውም ዓይነት ወረራ እንዳይነካና የኢትዮጵያዊነቱን እንደያዘ መቆየት አለበት የሚለውን የውጭ መንግሥታት አሳብ ከምንም አልቆጥረውም ማለትህና ወደፊትም ይህን አሳብ የምቀበል ሰው አይደለሁኝም ማለትህ ትክክለኛ ነህ፤ ጥሩም አድርገኻል፡፡
በተመሳሳይም አውሮፓዊው ጋዜጠኛው ቺሮ ፖጃሊ ፋሽስቶች የካቲት 13 ቀን 1929 ዓ.ም. በአራዳ ጊዮርጊስ ቤ/ክ ያደረጉትን ጭፍጨፋና ግፍ እንዲህ ዘግቦት ነበር፡፡
"ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤ/ክ ውስጥ ሰዎች መደበቃቸው ስለተሰማ ቤተክርስቲያኑ ውስጥ ቤኒዚን ተርከፍክፎ እሳት ተለቀቀበት፡፡ የቤተክርስቲያኑ ንዋያተ ቅድሳት፤ መጻሕፍትና ሥዕሎች በአጠቃላይ በእሳት ነደዱ፡፡ ከቤተክርስቲያኑ ውስጥ ከእሳቱ ለመሸሽ 50 ያህል ሰዎች ሲወጡ ተያዙና ከቤተክርስቲያኑ ጓሮ ተወስደው በቦምብ እንዲገደሉ ተደረገ፡፡"
የኢትዮጵያ ታላቅ ባለውለታ የነበሩትና የኢጣሊያን ፋሽስት ጭካኔና ግፍ ለዓለም ሁሉ በማጋለጥ ከኢትዮጵያውያን ጎን የቆሙት ሲሊቪያ ፓንክረስት- የፋሽስቱ መሪ ቤኒቶ ሞሶሊኒ በሃይማኖት አባቶች ላይ እየተወሰደ ያለው ርምጃ ሌሎች ኢትዮጵያውያንን ሊያሸማቅቅ እንደሚችልና ጭፍጨፋውም ውጤታማ እንደሆነ በወቅቱ ለምስራቅ አፍሪካ ለቅኝ ግዛት ሚ/ሩ ለግራዚያኒ ያስተላለፈውን ምስጢራዊ የቴሌግራም መልእክት ‹Ethiopia and Eritrea› በሚለው መጽሐፋቸው እንዲህ ጠቅሰውታል፡-
… The ex*****on of Abune Petros, one of the four Ethiopian bishops, has terrified the leaders and the public. The work of repression against armed groups dispersed in the forest continues. All prisoners have been shot. Inexorable reprisals have been effected against the populations guilty, if not complicity, at least of lack of favorable attitude. (A telegram of March 1, 1937)
ትርጉም፡- ‹‹በአቡነ ጴጥሮስ ላይ የተወሰደው የግድያ ርምጃ ብዙዎችን እንዲፈሩና እንዲሸማቀቁ አድርጓል፤ ይህ ዓይነቱ ርምጃ ለኢጣሊያን እንዳይገዛ ሕዝቡን በሚያነሣሡና በዱር በገደል በአርበኝነት በተሰማሩት ፋኖዎችም ላይ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባዋል…፤››
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤ/ክ በፋሽስት ለደረሰባት ግፍ፣ ጭፍጨፋ፣ ዝርፊያ… የኢጣሊያ መንግሥት ይቅርታ ሊጠይቅና ካሣ ሊከፍል ይገባዋል!!
ክብር ለኢትዮጵያ ነጻነት ሲሉ በግፍ ለተጨፈጨፉ ሰማዕታት!!
(Dn. Terefe W.)